Saturday, October 4, 2014

ዘመን ሲሸሽ – ዘመን ሲመጣ!


ዲቮሽን .21/2007 ረቡዕ፣ መስከረም 21/2007 ..
(
በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ


ዘመን ሲሸሽዘመን ሲመጣ!


እንግዲህ እንደ ጥበበኞች እንጂ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንዴት እንድትመላለሱ በጥንቃቄ ተጠበቁ፤ ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ (ኤፌ 515-16)

በደቡቡ የአገራችን ክፍል በሲዳማ ዞን ‹‹ጊጊሾ›› እና ‹‹ኮኬ›› የሚባሉ ሁለት ተመሳሳይ ዝርያ ኖሯቸው፣ ነገር ተቃራኒ ምኞት ያላቸው ወፎች አሉ፡፡ ‹‹ጊጊሾ›› የሚባለው ወፍ በአንዳንድ አካባቢዎች ‹‹ዘነበ›› በመባል ይታወቃል፡፡ የዚህ ወፍ ሳይንሳዊ ስሙ ‹‹ሬድ ቼስተድ ካኩ›› ይባላል፡፡

‹‹ጊጊሾ›› ወፍ የክረምቱን ወቅት አፍቃሪ ነው፡፡ ‹‹ጊጊሾ›› የክረምቱ ጊዜ ዘማሪ፣ የልምላሜው አብሳሪ ነው፡፡ ‹‹ጊጊሾ›› የበጋውን ጊዜ አይወድደውም፡፡ በበጋው ወቅት ያለበት ቦታ አይታወቅም፣ የኮቴው ኮሽታ አይሰማም፣ የድምጹ እልልታም አይደመጥም፡፡

 
ክረምቱ በበጋ መተካት ሲጀምር ‹‹ጊጊሾ›› የድምጹን ቮልዩም መቀነስ ይጀምራል፡፡ በክረምቱ ጊዜ የነበረው አረንጓዴውና ልምላሜው እየጠወለገ ሲሄድ ‹‹ጊጊሾ›› ድምጽም እየደበዘዘ መሄድ ይጀምራል፡፡ ከአቅጣጫው እየተፍቀለቁ ይፈስሱ የነበሩ የውሃ ምንጮች የፍሰት መጠናቸው እየቀነሰ ሄዶ መንጠባጠብ ሲጀምሩ፣ ‹‹ጊጊሾ›› ድምጽም ከመደመጥ ወደ አለመደመጥ ይወርዳል፡፡ በዝናቡ ረስርሶ፣ ረክቶና ረግቶ የነበረው መሬት መሰነጣጠቅ ሲጀምር፣ አቧራው እየቦነነ ከመሬት ወደ ሰማይ መበተን ሲጀምር ያኔ ‹‹ጊጊሾ›› ድምጹን ለወራት ያጠፋል፡፡ ‹‹ጊጊሾ›› የሚባል ወፍ ስለመኖሩ እንኳ እስኪረሳ ድረስ ድምጹ ድራሹ ይጠፋል፡፡

ነገር ግን የበጋው መጠናቀቂያ ጊዜ ሲደርስ ‹‹ጊጊሾ›› ድምጽ እንደገና ቀስ እያለ አልፎ አልፎ ሊደመጥ ይጀምራል፡፡ የበጋው የመጨረሻው የጸሐይ ትኩሳት ካባውን ደርቦ ስጋና ነፍስን ሲለበልብያኔ ‹‹ጊጊሾ›› ወፍ መቃተት ይጀምራል፡፡ አይኑን ወደ ሰማይ አንስቶ፣ አፉን በሰፊው ከፍቶ፣ ልብን በሚቀሰቅስ ስሜት ‹‹....›› የሚል የጣር ድምጽ ዝማሬ ማሰማት ይጀምራል፡፡

 
‹‹ጊጊሾ›› ድምጽ በሁሉም የምድሪቱ አቅጣጫ መደመጥ ሲጀምር የአገሩ አርሶ አደር ማረሻና ቀንበሩን ከሰቀለበት አውሮዶ መወልወል ይጀምራል፡፡ ለሚቀጥለው የመኸር ወቅት ቅድመ ዝግጅት ያደርጋል፡፡ ለወራት ተሰቅሎ የነበረውን የዘር እህል ቋጠሮ መፍታትና መፈተሽ፣ እንዲሁም ለመጪው የመኸር ስራ መንፈሱን ያነቃቃል፡፡

በዚህ ወቅት የአገሬው እንቦቃቅላ ሕጻናት ለወራት ተለይቷቸው የቆየው የዝናቡ ወቅት ተመልሶ ሊመጣ መሆኑን ‹‹ጊጊሾ›› ብስራት ስለሚረዱ በቃላት ሊገለጥ በማይችል ናፍቆት ውስጥ የሚወድቁበት ጊዜም ነው፡፡ ክረምቱ ደርሶ በንጹህ ሜዳ ላይ በሚተኛው የዝናብ ውሃ ላይ እየተንቦጫረቁ የሚጫወቱበትን ጊዜ በዓይነ ሕሊናቸው እየታያቸው በጉጉት እየተጠባበቁ ከጊጊሾ ጋር እየዘመሩ የሚናፍቁበት ወቅት ነው፡፡

‹‹ኮኬ›› የሚባለው ወፍ ደግሞ በተቃራኒ በጋውን ወቅት አፍቃሪ ነው፡፡ ‹‹ኮኬ›› የበጋው ወቅት ዘማሪ ነው፡፡ የክረምቱን ጊዜ አይወድደውም፡፡ በክረምቱ ወቅት ድምጹ አይሰማም፡፡ ክረምቱ ሲበረታ፣ ጫካና ገላጣው በዝናብ ሲታጠብ ያኔ ይከፋዋል፡፡ ክንፉን አንከርፍፎ፣ አንገቱን ቀብሮ፣ ጸጉሩን አንጨብሮ ማልቀስ ይጀምራል፡፡ የክረምቱ ወቅት አልፎ፣ ደመናው ተገፍፎ፣ ጉሙ ሰማዩን ሲለቅቅ፣ ጸሐይ ስትፈነጥቅ፣ ጭቃ ምድር ስትደርቅያኔ የእንጉርጉሮ ዝማሬውን ማሰማት ይጀምራል፡፡

 
የአገሬው አርሶ አደሮች በዚህ ወቅት ለመጪው የአጨዳ ወቅት የሚረዳቸውን ማጭድና መንሻቸውን ለወራት ከሰቀሉበት ቦታ አውርደው መወልወል ይጀምራሉ፡፡ ያረጀውን ጎተራ ማደስ፣ የተቦተረፈውን ጎተራ መጥቀም፣ በአረም የተዋጠውን አውድማ መጠራረግ፣ የዘመመውን ማድጋ ማቃናት ይጀምራሉ፡፡ መንፈሳቸውንም ያነቃቃሉ፡፡

ሕጻናቱም በአደይ አበባ ውስጥ ድብብቆሽ የሚጫወቱበት ጊዜ በዓይነ ሕሊናቸው እየታያቸው በናፍቆት ይቅበጠበጣሉ፡፡ እንጆሪና ሾላው፣ ጥንቅሽና ሸንኮራው፣ ባቄላና ቦይናው፣ በቆሎና ቦሎቄው አብበው፣ ጎምርተው፣ አሽተው፣ ተንዠርግገው የሚገምጡበትን ጊዜ እየናፈቁ አብረው ከኮኬ ጋር ይዘምራሉ፡፡

መንፈሳዊ ሰው እንደ ‹‹ጊጊሾ›› እና ‹‹ኮኬ›› ወፍ አንዱን ዘመን በደስታ፣ በእልልታና፣ በፌሽታ ተቀብሎ፣ ሌላው ዘመን ሲመጣ ግን ድምጹን አጥፍቶ፣ ተደብቶ፣ በሐዘን፣ በእንጉርጉሮና በእሮሮ ማሳለፍ የለበትም፡፡ መንፈሳዊ ሰው እንደ ታታሪ ገበሬ ሁሉንም ወቅት እንደ አመጣጡ ተቀብሎ በሚገባ ተጠቅሞበት ሊሸኘው ይገባል፡፡

 
ለሁሉ ጊዜ አለው፡፡ ለሁሉም ጊዜ ደግሞ ወቅት አለው፡፡ ሁሉም ወቅት ደግሞ የየራሱ የሆነ ብርቅዬ ዕድል አለው፡፡ ሁሉም ብርቅዬ ዕድሎች ብንጠቀምባቸው በረከት አላቸው፡፡ ሁሉም በረከቶች እርካታና ደስታ አላቸው፡፡ ሁሉም እርካታና ደስታ ደግሞ ምስጋናና ዝማሬ አላቸው፡፡

ስለሆነም ያለንበት ወቅት የሚመችም የማይመችም ሁኔታዎች አስከትሎ ቢመጣ እንደየአመጣጣቸው ተቀብለን እንድንሰራባቸው ጌታ ይርዳን፡፡ ዘመን ሲሸሽ ዘመን ሲመጣ በጊዜውም አለጊዜውም፣ በሚመችም በማይመችም ወቅት፣ ወገባችን ሳይላላ፣ ትጥቃችን ሳይፈታ፣ በሁኔታዎች ሳንረታ ዘመናችንን እንድንዋጅና ጊዜያችንን እንድንገዛ ጌታ ይርዳን፡፡

(ይህን ዕለታዊ ዲቮሽን ላይክ እና ሼር ያድርጉ፣ ወዳጅ ጓደኞችዎም እንዲያገኙ ያግዙ፡፡ ዲቮሽኑ ሳይቋረጥ ዓመቱን ሙሉ እንዲቀጥል በጸሎትዎና ጌታ በልብዎ በሚያስቀምጥ ማናቸውም ነገር ሁሉ ይደግፉ፡፡ ጌታ ይባርክዎ፡፡)

የጋብቻ አቀበት …የፈረሰ ይሁን!

ዲቮሽን .22/2007 ሐሙስ፣ መስከረም 22/2007 ..
(
በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


የጋብቻ አቀበትየፈረሰ ይሁን!


እርሱም፦ እግዚአብሔር መንገዴን አቅንቶልኛልና አታዘግዩኝ ወደ ጌታዬ እሄድ ዘንድ አሰናብቱኝ አላቸው።ርብቃንም ጠርተው፦ ከዚህ ሰው ጋር ትሄጃለሽን? አሉአት። እርስዋም፦ እሄዳለሁ አለች። እኅታቸውንምመረቁአትና፦ አንቺ እኅታችን፥ እልፍ አእላፋት ሁኚ ዘርሽም የጠላቶችን ደጅ ይውረስ አሉአት። ርብቃም ተነሣች ደንገጥሮችዋም፥ በግመሎች ላይ ተቀምጠው ያንን ሰው ተከተሉት …(ዘፍ 2456-61)

ከብዙ ዓመታት በፊት The Dirty Dozens በተሰኘ ፊልም ውስጥ የተመለከትሁትን ነገር ባስታወስኩ ቁጥር ልቤ ይነካል! በፊልሙ ውስጥ አንድ ከፍተኛ ደረጃ ያለው የጦር መኮንን፣ ለከፍተኛ ደረጃ ውትድርና የሚሰለጥኑ ሰዎችን ሲመለምል ያሳያል፡፡

አንድ ቀን ሰልጣኞቹ በገመድ እየተንጠላጠሉ ረዥም ከፍታ ወዳለው ማማ እንዲወጡ ታዘዙ፡፡ ጥቂቶቹ በስቃይ ማማው ላይ መውጣት ሲችሉ፣ አንዱ ግን መሃሉ ላይ ደርሶ ደከመውና መውጣት አቃተው፡፡ ለአለቃውም፣ ‹‹አልችልም›› ሲል ይነግረዋል፡፡ አሰልጣኙ ተኮሳትሮ ‹‹ትችላለህ›› ብሎ መለሰለት፡፡ ሰልጣኙ በደከመ ድምጽ በድጋሚ ‹‹አልችልም›› አለ፡፡

ሰልጣኙና አሰልጣኙ ‹‹ትችላለህ፣ አልችልም፣ ትችላለህ፣ አልችልም›› እየተባባሉ ሲጨቃጨቁ ጥቂት ሰኮንዶች አለፉ፡፡ በዚህም ምክንያት የተናደደው አለቃ፣ ከረዳቱ እጅ መሳሪያ በመንጠቅ ወደ ሰልጣኙ አቅጣጫ የጥይት እሩምታ ይተኩሳል፡፡ በዚህ ቅጽበት፣ ገመድ ላይ ደክሞትና እንደዚያ ዝሎና ተንጠላጥሎ የነበረው ሰልጣኝ፣ እንደ ጦጣ እየተስፈነጠረ ከማማው አናት ላይ ባንዴ ወጥቶ ጉብ አለና አማተበ፡፡

ታውቃላችሁ፣ በውስጣችን የታመቀ ኃይል አለ! በውስጣችን ያልታወቀ ብቃት፣ ያልተነካ ጉልበት አለ! አውጥተን ያልተጠቀምነው ስጦታ፣ ያልተገለገልንበት ችሎታ በውስጣችን አለ! ይህንን እውነታ ደግሞ ካመንን፣ በጋብቻ ላይ በአገራችን ያለውን ኋላቀር ባህል መድፈር እንችላለን፡፡ ወግና ልማዳችንን መስበር እንችላለን፡፡ እንደ ርብቃ፣ የሰርግና ድግስ ይሉኝታን አሽቀንጥረን መጣል እንችላለን፡፡ ማግባት እየፈለግን የሚያዘገየንን፣ ዕድል እያለን የሚያጨናግፈንን፣ ክብር እያለን የሚያዋርደንን፣ ሁሉ ማሸነፍ እንችላለን፡፡ ቤተሰብ ባይፈቅድ ቤተክርስቲያን አለን፣ የስጋ ዘመድ ባይቀበል መንፈሳዊ ዘመድ አለን፡፡

የአባይን ልጅ ውሃ ከጠማው፣ የላጭን ልጅ ቅማል ከበላው፣ ችግር አለ ማለት ነው! ግራና ቀኛችን በሚወድዱን ታጅቦ፣ ዙሪያ ገባችን በሰው ተከብቦ፣ ነገር ግን ለትዳር የሚሆን ሰው ከጠፋ እኛ ችግር አለ ማለት ነው!

ታውቃላችሁ፣ ስኬት የሚገኘው በፈተና ውስጥ ነው! ውቧ ጽጌረዳ እሾኻም ናት፡፡ ጣፋጭ ማር ሰጭ ንብ መርዝ አላት፡፡ ዓሳም አጥንት አላት፡፡ ብርቅዬ ማዕድናት የሚገኙት ከድንጋይ ውስጥ ነው፡፡ ወርቅና ብረት የሚወጣው ከአፈር ውስጥ ነው፡፡ ትዳር የሚገኘው ከሰው መካከል ነው፡፡

ወገኖች ሆይ፣ አለት ተደርምሶ ማዕድን ከወጣ፣ አፈር ተቆፍሮ ብር ወርቁ ከወጣ፣ ከሰው ተፈልጎ እንዴት ትዳር ይታጣል? መፈቀር ሳያንሰን፣ ማፍቀር ሳያቅተን፣ መውደዱ ሳይቸግር መወደዱም ሳለ፣ ትዳር እንዴት ተራራ ይሆናል? ጠባይና ውበት፣ ችሎታና እውቀት ሳያንስ፣ እህልና ውሃ ሳይቸግር፣ ትዳር ምስረታው እንዴት ዳገት ይሆናል? ሰው ትዳር መያዝ እየፈለገ ለምን ያቅተዋል?

ክልላዊነትና ቀበሌያዊ አስተሳሰብ ለበርካታ ወገኖቻችን ትዳር እንቅፋት ሆኖ ቆይቷል፡፡ በርካታ ምዕመናን ይህንን አስተሳሰብ ጥሰው መውጣት አልቻሉም፡፡ በጌታ አምነው የዳኑ በርካታ ክርስቲያን ወንድሞችና እህቶች እንኳ ጋብቻ ለመመስረት በዘር፣ በወንዝና በቁሳቁስ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ተንጠላጥለው ይታያሉ፡፡ ብዙዎቹ የቤተሰቦቻቸውን ፈቃደኝነት ይጠብቃሉ፡፡ በርካታ የአገራችን ቤተሰቦች ደግሞ ጠባብ አስተሳሰብ አላቸው፡፡ ለትዳር ምስረታ ቅድመ ሁኔታዎች ያስቀምጣሉ፡፡ ሀብትን፣ ዘርን፣ ባህልን መሠረት አድርገው ይሁንታ ይሰጣሉ፣ ወይም ይነፍጋሉ፡፡

በተለይም እህቶች ጋብቻን ለራሳቸው ሳይሆን ለቤተሰቦቻቸው ሲሉ የሚመሰርቱ ይመስላል፡፡ በአገራችን ስለጋብቻ ሲታሰብ ሰርግ፣ ስለ ሰርግ ሲታሰብ ደግሞ ድግስ፣ ድግስ ሲታሰብ ደግሞ አሸሼ ገዳሜው ይታሰባል! ለብዙዎቻችን ድንኳን ካልተተከለ፣ ቡፌ ካልተደረደረ፣ ጮማ ካልተቆረጠ ቅልጥም ካልተገሸለጠ ጋብቻው ጋብቻ አይመስለንም፡፡ ተጋቢዎች ይህን ለማሟላትም፣ አቅም ስለሚያንስ ለዓመታት መቆየት ይገደዳሉ፡፡ አንዳንዶቹም የማይችሉት ይሆንና ወዳሰቡበት ሳይደርሱ ተሰናክለው ይወድቃሉ፡፡ አንዳንዶቹ በሰው ምርጫ ሳይሆን በቁሳቁስ ምርጫ ላይ ዘመናቸውን ጨርሰው ወደኋላው ዘመን ይቆጫሉ፡፡

አንዳንድ ጀግና እህቶች ደግሞ አሉ፡፡ እንደ ርብቃ የቆረጡሌሞዚን ካልመጣ፣ መርቼዴስ ካልወጣ የማይሉ! ጋብቻን ለመመስረት፣ ቪላ ካልተሰራ፣ መኪና ካልተገዛ፣ ብለው የማያመቻምቹ! እማዬ፣ አባዬ፣ እህትዬ ጋሼ እያሉ በገዛ ምርጫቸው ላይ የማይልፈሰፈሱ! አጃቢ አነሰ፣ ሰርገኛው ቀነሰ የማይሉ እንደ ርብቃ ያገኙትን ይዘው፣ በቀረበው ነገር ተሳፍረው የሚሄዱ!

የጋብቻ አቀበት፣ የባህልና የይሉኝታ ሰንሰለት በኢየሱስ ስም የተመታ ይሁን! ከሚቀርቡን ፊት የሚያሸሸን፣ ከሚሸሹን ኋላ የሚያሮጠን መንፈስ በጌታ በኢየሱስ ስም የተመታ ይሁን! የትዳር ፈተና፣ የኑሮ ቀንበር፣ የተሰበረ ይሁን! ልብን ትቶ መልክን፣ መንፈስን ጠልቶ ስጋን የሚያስወድድ ባህላዊ የሰው መስፈርት የተሰበረ ይሁን፡፡ ለሰርግና ድግስ፣ ለብር ለቁሳቅስ ጋብቻን የሚያዘገይ መንፈስ የተሰበረ ይሁን! ትዳርን በሀብት ላይ፣ በመልክና ዘር ላይ የሰቀለ መንፈስ የተመታ ይሁን! ጋብቻን የሚያጠብብ ክልላዊ ግድብ፣ ቀበሌያዊ ምድብ የፈረሰ ይሁን! በጌታ በኢየሱስ ስም የጋብቻ አቀበት የተናደ ይሁን! ይህ ዓመት የጋብቻ ዓመት ይሁን!