Saturday, February 28, 2015

የጨለማ ሽንፈት!

ዲቮሽን .170/07፣ አርብ የካቲት 20/07 ..
(
በፓ/ር ተስፋሁን ሐጢያ)


የጨለማ ሽንፈት!

ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም (ዮሐ 15)

የብሉይ ኪዳኑ ነቢይ ኢሳይያስ (92) እንደተነበየው፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህች ምድር ሲመጣ፥ "በጨለማ ይሄድ የነበረው ሕዝብ ብርሃን አየ፥ በሞት ጥላ አገርም ለሚኖሩ ብርሃን ወጣላቸው፡፡

ወገኖች ሆይ፥ ጌታችን ኢየሱስ ወደዚህ ምድር የመጣው መንፈሳዊ ብርሃን ሊሰጠን ነው፡፡ መንፈሳዊ ጭለማን ገፍፎ፥ መንፈሳዊ ብርሃን ሊሰጠን! ኦ፥ ሃሌሉያ! ጌታ ወደ ሕይወታችን የገባው ጨለማችንን ገፍፎ፥ በጨለማ ውስጥ ብርሃን ይሁን ሊል፥ የጨለማን ስራ ሊያፈርስ፥ በብርሃን እንድንመላለስ ነው!

ጌታን ስንቀበል ውጦን የነበረው ትብታብ፥ ጫካና አረንቋው፥ የአጋንንት ስንክሳር፥ ጥንቆላ መተቱ፥ አፍዝ አደንግዙ፥ በጌታ ኢየሱስ ብርሃን መታሰቢያው ጠፍቶ ነጻ እንድንወጣ ነው!
ታውቃላችሁ፥ ብርሀኑ በጨለማ ሲበራ ጨለማ አያሸንፈውምና፥ በዘር በግንዳችን፥ በደም በስጋችን፥ በአቻ ጋብቻችን የተጣበቀብን የጨለማ መንፈስ ድራሹ ይጠፋል! የአባት የአያታችን፥ ቅማያት ምንጅላት ምንትስ ያደረጉት ኪዳን፥ የፈጸሙት መሃላ፥ የቀረጹት ጣዖት፥ የተከሉት ሐውልት፥ ብትንትኑ ይወጣል!

ታውቃላችሁ፥ ጌታን ስንቀበል፥ የኢየሱስ ብርሃን በእኛ ላይ ሲበራ፥ "ወልጄ አሳድጌ፥ ወግ ማዕረግ አድርሼ፥ ለፍቻለሁና አልለቀውም እያለ የሚጎርር መንፈስ በዝረራ ይወድቃል! ሃሌሉያ!

ታውቃላችሁ፥ በሕይወታችን ላይ ብርሃን በርቷልና፥ አወቅን አላወቅን፥ ገባንም አልገባን፥ እኛን እንዲያጠፋ የተላከ መንፈስ፥ ጠንቋይ ሞራ ገላጭ፥ ሰላቢ ገጣቢ፥ ፈልፈላ ድግምቱን ኤልሻዳዩ ጌታ ከእግራችን በታች ጥሎ ይረግጠዋል!

ታውቃላችሁ፥ ብርሃኑ ሲበራ እርግማን ነጋሪ፥ ጨረር አስቀባሪ፥ ኮረኮንች ወርዋሪ፥ ኮከብ አስቆጣሪ፥ መድሀኒት ቀማሚ፥ ጥላ ወጊ መንፈስ በጌታ በኢየሱስ ተመትቶ ይወድቃል! በያዕቆብ ላይ አስማት፥ በእስራኤልም ላይ ሟርት የለምና፥ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ የጨለማ ስራ በፍጹም አይሰራም!

ወገኖች ሆይ፥ የኢየሱስ ብርሃን በእኛ ላይ ከበራ፥ ተኛንም ተነሳን፥ ነቃንም አልነቃን፥ ሕዝቡን የሚጠብቅ አይተኛም፥ አያንቀላፋምና የጨለማ ስራ ሊያሰጋን አይችልም!


ታውቃላችሁ፥ ብርሃኑ በጨለማ ሲበራ፥ ጨለማ አያሽንፈውምና በዙሪያችን ያለ የትኛውም ጨለማ ይህን ብርሃን ማቆም፥ ኢየሱስን መቃወም፥ በጨለማው ግዛት ወንጌል እንዳይሰበክ፥ ምርኮ እንዳይማረክ ማገድ፥ መገዳደር በፍጹም አይችልም!

የጥበብና የመገለጥ መንፈስ!

ዲቮሽን .171/07፣ ቅዳሜ የካቲት 21/07 ..
(
በጌታሁን ሓለፎም)


የጥበብና የመገለጥ መንፈስ!

‹‹የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብን እና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ›› (ኤፌ 1:17)፡፡

ይህ መልእክት ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፈሶን ቤተክርስቲያን እና በዚያን ዘመን በአካባቢው ላሉ ምእመናን እየተዘዋወረ እንዲነበብ ታስቦ የጻፈው ደብዳቤ ነው:: ምእመኑ ዲያና (አርጠምስስ ) ትባል ከነበረች የጣኦት አምልኮ ፊቱን አዙሮ ክርስቶስን በማመን እና እርስ በርስ በመዋደድ ያሳየው እድገት መልካም ነበር፡፡ ይህ መልእክት እግዚአብሔር ምእመኑን ወደ በለጠ ከፍታ ይዞአቸው እንዲገባ የጸለየበት እና የቃተተበት መልእክት ነው::

እግዚአብሔርን በማወቅ የጥበብ እና የመገለጥ መንፈስ እንዲሰጣችሁ እጸልያለሁ፡፡›› እግዚአብሔርን በጥቂቱ እንዳታውቁት ሌላ ብዙ የከበረ እቅድ እና ፕሮግራም ለናንተ አለው:: በቅድስናና ያለ ነውር እንድትሆኑ ታስቦ ነው በክርስቶስ የተፈጠራችሁት፣ ስለዚህ ነውርን አርቁ::

እግዚአብሔር በሰማይ ያዘጋጀላችሁ ስፍራ የከበረ ነው እና ነገራችሁን ምድራዊ በሆነ ከንቱ ነገር አትለኩት፡፡ የጌታ የሃይሉ ታላቅነት የቱን ያህል እንደሆነ እወቁ እንጂ አትፍሩ፣ አትደንግጡ፡፡ የትንሳኤው ሃይል ሙታንን ያስነሳ፣ መቃብርን የፈነቀለ ዲያቢሎስን የረታ ነውና በጌታ ታመኑ፣ ጽኑ::

የሽንፈት ኑሮ አትኑሩ! ጌታን ማወቃችሁ መልካም ነው፣ ነገር ግን ሌላ ክብር አለ! ሌላ እውቀት አለ! ሌላ ከፍታ አለ! ያን ለማየት ደግሞ የልቦናችሁ አይኖች እንዲከፈቱ ያስፈልጋል::

ወገኖቼ፣ ይህ ደብዳቤ አሁን የኛ ደብዳቤ ነው:: በዚህ ዘመን ለምንኖር አማኞች የተጻፈ መልእክት ነው! የተጠራንበት አላማ ሊገባን ያስፈልጋል:: ከመብላት፣ ከመጠጣት፣ ከመልበስ ያለፈ የዘላለም ክብር እግዚአብሔር ለእኔ እና ለእናንተ እንዳለው መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ስብከታችን፣ መልእክታችን፣ ኑሮአችን ምድርን ያማከለ እንዳይሆን፣ የልቦናችን አይኖች ተከፍተው፣ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንደሆነ ልናውቅና ልንረዳ ያስፈልጋል!
--------------------------------

(ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክ ያድርጉ፣ ጌታ ይባርክዎ!)