Saturday, January 17, 2015

የመግለጥ – አገልግሎት (#1)!

ዲቮሽን .129/07     ቅዳሜጥር 9/07 ..
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


የመግለጥ – አገልግሎት (#1)! 

አሁን ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ወደ እናንተ መጥቼ በልሳኖች ብናገር፥ በመግለጥ ወይም በእውቀት ወይም በትንቢት ወይም በትምህርት ካልነገርኋችሁ ምን እጠቅማችኋለሁ?(1ቆሮ 14፡6)፣ … ደግሞ የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታውቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ ስለ እኔ ለምኑ፤ ስለ ወንጌልም በሰንሰለት መልእክተኛ የሆንሁ፥ መናገር እንደሚገባኝ ስለ እርሱ በግልጥ እናገር ዘንድ ለምኑ (ኤፌ 6፡19-20)፡፡

ሐዋርያው ጳውሎስ ከላይ በቀረቡ ጥቅሶች ውስጥ የተናገራቸው የመግለጥ ዓይነቶች ሁለት ናቸው፡፡ ከነርሱም፣ አንደኛው ‹‹የወንጌል ምስጢር›› ሲሆን ሁለተኛው ‹‹የእግዚአብሔር ምስጢር›› ተብለው የተጠቀሱ ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ‹‹መግለጥ›› ነባራዊ የሆነውን የወንጌልን ምስጢር ተርትሮ የመስበክን ወይም የማስተማርን ብቃት ሲያመለክት፣ ሁለተኛው ‹‹መግለጥ›› ደግሞ ቅጽበታዊ የሆነውን እግዚአብሔር ለሕዝቡ የሚገልጠውን ምስጢር ተረድቶ ለሰው የማስተላለፍ ችሎታን ያመለክታል፡፡

ታውቃላችሁ፣ አንድ አገልጋይ ‹‹ባለመግለጥ›› ሊባል የሚችለው እነዚህን ሁለቱን ነገሮች አጣምሮ፣ ወይንም ከሁለቱ አንዱን ይዞ ሲገኝ ነው!

ታውቃላችሁ፣ ‹‹መግለጥ›› ማለት እግዚአብሔር ለልጆቹ መግለጥ የሚፈልገውን ነገር አጉልቶ ማሳየት፣ ዘርዝሮ ማብራራት እና ተንትኖ ማስረዳት ነው!

ታውቃላችሁ፣ ‹‹መግለጥ›› ማለት የወንጌልን ምስጢር በግልጥ ማስታወቅ፣ የተገለጠውን ነገር በድፍረት መናገር፣ ያለፍርሃት ማስታወቅ፣ ያለፍርሃት ማስተላለፍ ነው!

ወገኖች ሆይ፣ የመግለጥ አገልግሎት በተፈጥሮው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚጠይቅ ነው! ከፍተኛ የሆነ ጥንቃቄ ካልተደረገበት አገልግሎቱ በቀላሉ ለስህተት የመጋለጥ ዕድሉ የሰፋ ነው!

ወገኖች ሆይ፣ ‹‹አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ›› እንዲሉ፣ በአገራችን ካለው ካልዳበረው የመግለጥ አገልግሎት የተነሳ በአጠቃላይ የመግለጥ አገልግሎቱን ልናንቋሽሽ አይገባም፡፡ የሰውን ልምድ ከእግዚአብሔር ቃል እውነት ለያይተን መመልከት መቻል ይኖርብናል፡፡ በመግለጥ አገልጋዩ በኩል የአያያዝ ችግር ወይንም ስህተት ቢገኝ፣ ‹‹ከአያያዝ ሊቀደድ…›› መቻሉ ያለና የሚኖር እውነት መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል!

ታውቃላችሁ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊው እውነት ቋሚና ከስህተት ነጻ ሲሆን፣ የሰው ልምድ ግን ተለዋዋጭና ለስህተት የተጋለጠ ነው! ስለሆነም፣ መጽሐፍ ቅዱስን በሰው ልማድ መተርጎም አደገኛ ነው!

ወገኖች ሆይ፣ ልማዳችንን መሠረት በማድረግ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን የምንተረጉም ከሆነ ለስህተት አሰራር ልንጋለጥ እንችላለን፡፡ ከዚህም የተነሳ፣ ለቃሉ ታማኝ ሆኖ በማገልገል ከሚገኘው መለኮታዊ በረከት ሳንካፈል እንቀራለን፡፡ በተጨማሪም፣ ልምምዳችንን ለቃሉ ሥልጣን ባለማስገዛታችን ምክንያት አንድ ቀን በእግዚአብሔር ፊት ምላሽ እንሰጣለን!
-----
ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክ ያድርጉ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!

--------------------------------

‹‹የወንጌላዊ እጮኛ›› አዲስ መጽሐፍ፣ በገበያ ላይ ውሏል፡፡ ለተጨማሪ መረጃ በ0911 678158 ወይም 0911 813092 ይደውሉ፡፡

ከተቀቡ - ይወገራሉ!

ዲቮሽን .128/07 አርብ፥  ጥር 8/07 .
(
በፓ/ ተስፋሁን ሐጢያ)


ከተቀቡ - ይወገራሉ!

እስጢፋኖስም ጸጋንና ሀይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበርአንዳንዶቹ ተነስተው እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር፥ ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉምየናዝሬቱ ኢየሱስ ይህን ስፍራ ያፈርሰዋል፥ ሙሴም ያስተላለፈልንን ስርዓት ይለውጣል ሲል ሰምተነዋልና የሚሉ የሐሰት ምስክሮችን አቆሙ (የሐዋ 68-15)

እስጢፋኖስ መልካም ምስክርነት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የተሞላ፥ እምነትና ጥበብም የሞላበት ሰው ነበር፡፡ በነዚህ ማንነቱ ምክንያት እስጢፋኖስ ከሌሎች ሰባት ሰዎች ጋር ለድቁና አገልግሎት ተመረጠ! የድቁናው ምርጫ ያስፈለገበት ምክንያት በምግብ ማደል አሰራር ላይ ለተፈጠረው ማጉረምረም መፍትሔ እንዲሆን ነው፡፡

ወገኖች ሆይ፥ የምዕመናን ቁጥር እየበዛ ሲሄድ፥ የግሪክ ቋንቋ ተናጋሪ የሆኑት አይሁድ ማጉረምረም ጀመሩ! ምክንያታቸውም፥ በየዕለቱ ምግብ በሚታደልበት ጊዜ ባሎቻቸው ለሞቱባቸው ግሪክ ተናጋሪ አይሁድ ሴቶች የሚሰጠው ምግብ፥ ባሎቻቸው ለሞቱባቸው ዕብራይስጥ ተናጋሪ የአይሁድ ሴቶች ከሚሰጠው ያነሰ ነው፥ የሚል ክስ ነው!

ወገኖች ሆይ፥ እስጢፋኖስ የምግብ እደላውን ፍትሐዊ ለማድረግ እምነት ከተጣለባቸው ሰባት ሰዎች አንዱ ነበረ፡፡ በዚህ አገልግሎቱ ቀደም ሲል ተፈጥሮ የነበረው ጉርምርምታ ዳግመኛ አለመደመጡም ሆነ ስሙን በክፉ የሚያነሳ ሰው አለመገኘቱ እስጢፋኖስ በድቁና አገልግሎቱ ስኬታማ እንደነበር መናገር ይቻላል!

ታውቃላችሁ፥ የእስጢፋኖስ ስም በክፉ መነሳት የጀመረው ጸጋና ሀይል ተሞልቶ እጅግ አስደናቂ የሆኑ ተአምራትን በሕዝቡ ፊት ማድረግ ሲጀምር ነው!

ታውቃላችሁ፥ በሕይወታችን ጸጋና ተአምራት፥ ድንቅና ምልክት መሆን ሲጀምር ክርክር ይነሳል! ተራ አባል ሆነን ያልተወራ ወሬ፥ ቅባት ተቀብለን ማገልገል ስንጀምር መጦዝ ይጀምራል! ተራ ምዕመን ሆነን ያልተሰማ ዜና፥ ድንቅና ምልክት ማድረግ ስንጀምር የሰበር ይሆናል!

ታውቃላችሁ፥ ተቀብቶ መውጣት ሰልፈኛ ያስነሳል! ድንቅና ምልክት ማድረግ ክርክር ያመጣል! ጥበብና መንፈስ መግለጥ ተቃውሞ ያስነሳል!

ታውቃላችሁ፥ ቅባት ተቀብሎ በቅባት ማገልገል ቅናት ይቀሰቅሳል፥ በሐሰት ያስከስሳል፥ ውግዘት ያስከትላል!

ወገኖች ሆይ፥ ቅባት ተቀብሎ በቅባት ማገልገል ቅናት ምቀኝነት ክፉ ወሬ ብቻ ሳይሆን፥ ክርክር ጭቅጭቅ የሐሰት ክስ ብቻ ሳይሆን፥ መወገር፥ መደብደብ፥ መሰቀል ያመጣል!

-------
ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክ ያድርጉ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!