Saturday, June 13, 2015

ኃይሌ!!!!

ዲቮሽን 277/07 እሁድ ሰኔ 7/07
(በእህት ማርታ ሲሳይነህ)

ኃይሌ!!!!

“ጌታ እግዚአብሔር ኃይሌ ነው!” ዕንባቆም 3፡19

አንዳንዴ ያለንበት ነባራዊ ሁኔታ፣ ወይም የተጫነን ወቅታዊ ስሜት፣ በስጋችንም በነፍሳችንም ዝለት እንዲሰማን
ያደርጋል። አስተዳደጋችን፣ እድሜያችን፣ የትምህርት ደረጃችን፣ የምናሳየው ባህሪ፣ የተሰበክነው ስብከት፣ ያነበብናቸው መጻህፍት፣ ያለንበት መልክዓምድራዊ አቀማመጥ፣ ሰዎች እንዲህ ናችሁ ብለው ያስቀመጡብን ስያሜ፣ ብቻ እጅግ በጣም እልፍ አእላፋት ነገሮች ---- ተጠራቅመው፡ ‘አልችልም፤ እኔ እንዲህ አይደለሁም፤ ይህን ለማድረግ ብቃት የለኝም፣ ይህ ሁኔታ ከባድ ነው’፣ እና የመሳሰሉትን አሉታዊ ነገሮች በራሳችን ላይ እንድናውጅ ያደርጉናል።

ግን ዕንባቆም ሲናገር እንዲህ አለ፡- ጌታ እግዚአብሔር ኃይሌ ነው፣ እግሮቼን እንደ ዋላ እግሮች ያደርጋል፣ በከፍታዎችም ላይ ያስሄደኛል። ዕንባቆም 3፡19

ዳዊትም ሲናገር: 2 ሳሙ 22: 34 እግሮቼን እንደ ብሆር እግሮች የሚያበረታ፥ በኮረብቶችም የሚያቆመኝ
እግዚአብሔር ነው።

ዛሬ፣ ለኔም ሆነ ለእናንተ ይህ የእንባቆም እና የዳዊት መንፈስ እንዲገባብን ጸሎቴ ነው። “ጌታ እግዚአብሔር ኃይሌ ነው! በአምላኬ ቅጥሩን እዘላለሁ።” እንድትሉና፣ እንድታደርጉትም ይኼው ጸለይኩ።

ከፍ ካሉብን ነገሮች በላይ እግዚአብሔር ያስኬደናል፣ ዳገት ከሆኑብን፣ ተራራ ከሆኑብን፣ ካደከሙን እና ካሰለቹን ነገሮች በላይ እግዚአብሔር ትልቅ ነው። እግዚአብሔር ኃይላችን ነው፣ ብርታታችን ነው።

መንፈስ ቅዱስ ሆይ፣ አንተ ብርቱና ኃያል መሆንህን ነፍሳችን እንድታውቅ፣ ዛሬ በእያንዳንዳችን ላይ ና! ኢየሱስ ሆይ፣ የሚያበረታው መንፈስህ፣ ኃይል የሚሰጠው መንፈስህ ይውረድብን፣ እንደሌላ ሰው የሚያደርገው፣ ከልማድ ህይወት የሚያስወጣው፣ ከልማድ ኃጢያት እና ድካም የሚያዘልለው ያንተ ኃይል፣ አ----ሁ----ን ይፍሰስብን። ሰምተህኛልና ተባረክ። ኦ! ሀሌ ሉያ!!!!

ትምህርቱ ጠቅሞዎታል? እንግዲያውስ እባክዎ፣ ላይክ እና ሼር፣ ኮሜንትም ያድርጉ ። ጌታ ይባርክዎ!

ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ

 ዲቮሽን 276/07 ቅዳሜ ሰኔ 6/07
(በዶ/ር በቀለ ብርሃኑ)



ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ የእግዚአብሔር ቃል “አንተ ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ፡-አቤቱ ፊትህን እሻለሁ፤ልቤ አንተን አለ” (መዝሙር 27፡8) ብሎ ይናገራል፡፡ይህ አገላለጽ እጅግ ግሩምና ጥልቅ ነው−የአባትና የልጅ መሻት የተገናኙበት! በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ መናፈቅ፣መፈለግ፣መሻት፣መጠማት፣መራብ የሚሉ ቃላት እጅግ የተወደዱ ናቸው፤በረከታቸውም እጅግ ሰፊ ነውና፡፡በተለይ መዝሙረ ዳዊት በነዚህ ዓይነት ሐሳቦች ታጭቋል፡፡ለአብነት አራቱን ላሳያችሁ፡- • “ነፍሴ የእግዚአብሔርን አደባባዮች ትወድዳለች ትናፍቅማለች፤ልቤም ሥጋዬም በሕያው አምላክ ደስ ተሰኘ”(መዝሙር 84፡2) • “አምላኬ፥ አምላኬ፥ ወደ አንተ እገሠግሣለሁ፤ ነፍሴ አንተን ተጠማች;ሥጋዬ አንተን እንዴት ናፈቀች እንጨትና ውኃ በሌለበት በምድረ በዳ”(መዝሙር 63፡1) • “እግዚአብሔርን አንዲት ነገር ለመንሁት እርስዋንም እሻለሁ፤ በሕይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ፣ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኘውንም አይ ዘንድ፣መቅደሱንም እመለከት ዘንድ”(መዝሙር 27፡4) • “ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፥ አቤቱ፣እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች። ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ?” (መዝሙር 42፡1-2) በግሌ የንጉሥ ዳዊትን በተለይ“አፌን ከፈትሁ አለከለክሁም ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና” (መዝሙር 119፡131) የሚለውን የመሻት አገላለጽ ባነበብኩት ቁጥር ልቤ በኃይል ነው የሚነካው፡፡እንዲህ ዓይነቱ ሐሳቦች፣ንጉሥ ዳዊት እግዚአብሔርን በመሻት ማቆሚያ የሌለው መንፈሳዊ በረከት ውስጥ እንደ ነበረ በሚገባ ይጠቁማሉ፡፡ የተጻፉት ሁሉ ለትምህርታችን ተጽፈዋልና፣በክርስትና ሕይወታችን እግዚአብሔርን መሻት ትልቅ ዋጋ ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡መሻት ደግሞ መፈለግን ይወልዳል፤መፈለግ ደግሞ በማግኘት ይተካል፡፡ከብዙ ፍለጋ በኋላ የራበውንና የጠማውን ነገር ያገኘ ሰው ደግሞ ልቡ በደስታ እንደሚዘል ምን ጥርጥር አለው?! ውስጡ ወደ ኋላ በማይመለስ መልኩ ተለውጦ ይቀራልና፡፡ይህንን ሐሳብ በተሰናሰለ መንገድ ላስቀምጠው፡- መሻት(desire)-------›መፈለግ(seek)-------›ማግኘት(find)-------›ደስታ(joy) በነገራችን ላይ መንፈሳዊ መሻት እጅግ የሚቀጥልና እያደገ የሚሄድ ነገር ነው፤ካንድ ደረጃ ወደ ሌላ ደረጃ ይሻገራል እንጂ በፍጹም ማቆሚያ የለውም፡፡በእንደዚህ ዓይነት ሕይወት ውስጥ ያለች ነፍስ ደግሞ፣ልክ በድግስ እንደሚበሸበሹ ሰዎች ቋንቋ በማይገልጸው ደስታ፣ግርምትና አድናቆት ስትዘልል ውላ ታድራለች፤ለምን ቢባል ዳዊት ከብዙ ግሥገሣና መሻት በኋላ “ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች፤ከንፈሮቼም ስምህን በደስታ ያመሰግናሉ”(መዝሙር 63:5)ያለው ቅኝት ይፈጸማልና ነው፡፡ አዎ፣እግዚአብሔርን መሻት የመንፈሳዊ በረከቶች ሁሉ ምንጭ ሲሆን፣እኛ በሥጋዊ አካሄዶች ካልገታነው በቀር የሚቆም ነገር አይደለም፡፡እየጋለና ከእግዚአብሔር ጋር እንድንጣበቅ፣ከጉያው እንዳንጠፋና በመንፈሳዊ ሕይወታችን እንድናድግ፣እንድንጠነክር፣እንድንበረታና ለሌሎችም በረከት የሚያደርግ ርምጃ ነው፡፡ በግሌ እንዳየሁት እግዚአብሔርን ከምር የሚሻ ሰው፣ድሪሟ እንደጠፋባትና እስክታገኘው ድረስ እንደ ፈለገችው (ሉቃስ 15፡8-9) ሴት ሳያሰልስ በቆራጥነት ይሻል፣ይተጋል፣ይፈልጋልም፡፡እስከሚያገኝና ልቡ በሐሤት እስኪጥለቀለቅ ድረስ እረፍት አይኖረውም፡፡አዎ፣እግዚአብሔርን የሚሻ ሰው ጊዜውን፣ገንዘቡንና ኃይሉን ሁሉ ለመሰዋት ወደ ኋላ አይልም፣አይሰስትም፡፡ረብ የሌላቸውንና ከጉዞው የሚጐትቱ አደናቃፊ ነገሮች ጥሶ ለመሄድ በነፍሱ ላይ ርምጃ ይወስዳል፣አይሳሳምም፡፡ በብዙ የእግዚአብሔር ሰዎች እንደ ተመሰከረው የሚፈልግ ሰው ደግሞ ማግኘቱ አይቀርምና የሚገኘው መለኮታዊ ደስታ ከአእምሮ በላይ ነው የሚሆነው፤ምክንያቱም ቃሉ “እግዚአብሔርን የሚፈልጉ ሰዎች ከመልካም ነገር አይጐድሉም” (መዝሙር 34፡10) ይላልና! ነቢዩ ኤርምያስ ከብዙ ፍለጋ በኋላ “ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ፤ አቤቱ፣የሠራዊት አምላክ ሆይ፣በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ ” (ኤርምያስ 15፡16) አይደል ያለው? ስለሆነም ወገኖቼ እባካችሁ፣እኛም እንደዚህ ነቢይ ነፍሳችን በሐሤት እስክትጥለቀለቅ ድረስ፣ተግተን እንሻው፣እንፈልገው! “እናንተ ትሹኛላችሁ፣በፍጹም ልባችሁም ከሻችሁኝ ታገኙኛላችሁ።ከእናንተም ዘንድ እገኛለሁ ይላል እግዚአብሔር” (ኤርምያስ 29፡13)