Thursday, December 18, 2014

ኃይልን በእምነት ማግኘት !

ዲቮሽን .99/07     ሐሙስ ታህሳስ 9/07 ..
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


ኃይልን በእምነት ማግኘት !

ተስፋ የሰጠው የታመነ እንደ ሆነ ስለ ቈጠረች፥ ሣራ ራስዋ ደግሞ ዕድሜዋ እንኳ ካለፈ በኋላ ዘርን ለመፅነስ ኃይልን በእምነት አገኘች። ስለዚህ ደግሞ በብዛታቸው እንደ ሰማይ ኮከብ እንደማይቈጠርም በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ የነበሩት የሞተን ሰው እንኳ ከመሰለው ከአንዱ ተወለዱ (ዕብ 11፡11-12)።

ሳይንሱ እንደሚጀነጅነን ሴቶች ከአርባዎቹ የዕድሜ ክልል ጀምሮ የመውለድ ዕድላቸው እየቀነሰ ይሄዳል፡፡ በሴቶች የሚሆነውም ልማድ በእነዚህ ዓመታት ክልል ውስጥ መቋረጥ ይጀምራል፡፡ ከዚህ ታሪክ በኋላ ልጅ መውለድ የማይታሰብ ይሆናል፡፡ ይህ አስተሳሰብ ‹‹ሳይንሳዊ ሐቅ›› ይባላል!

ወገኖች ሆይ፣ ይህ ‹‹ሣይንሳዊ ሐቅ›› ሳይንሳዊ ሐቅ እንጂ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሐቅ አይደለምና፣ በእምነት ላቦራቶሪ ፍተሻ ሲደረግ ‹‹ፉርሽ ሐቅ›› ሆነ! ስለሆነም፣ ከሣይንሳዊ ጥናት ውጭ፣ ከሙያዊ መላምት ውጭ፣ ከሰዋዊ አስተሳብ ውጭ በሆነ ሁኔታ አብርሃምና ሣራ በዕድሜአቸው ሸምግለው ፈጽመው አርጅተው ሳሉ ኃይልን በእምነት አገኙ!

ታውቃላችሁ፣ ተስፋ የሰጠው የታመነ እንደ ሆነ ስለ ቈጠረች፣ ሣራ እግዚአብሔር ታመነች! ዕድሜዋ አልፎ እንኳ፣ ነገሯ ኤክስፓየር አድርጎ እንኳ ተስፋ የሰጠው የታመነ ነውና፣ እግዚአብሔር ታመነች!  አርግዞ ለመውለድ፣ ወልዶም ለማሳደግ ኃይልን በእምነት አገኘች!

ወገኖች ሆይ፣ አሮጊቷ ሣራ እግዚአብሔር ስለታመነች፣ ኃይልን በእምነት አገኘች! ከዚህም የተነሳ፣ የአሮጊቷ ማህጸን ልጅ መሸከም ቻለ! ይህም ብቻ አይደለም፣ አሮጊቷ ስትወልድ ሰበር ዜና ሆነ! ይህም ብቻ አይደለም፣ የአሮጊቷ ጡቶች በወተት ተሞልተው ልጅን ሲያጠቡ በሰዎች መካከል መደነቅ፣ መገረም መሣቅ መነጋገር የሀገር ሥራ ሆነ!

ወገኖች ሆይ፣ ኃይልን በእምነት ያገኙት አብርሃምና ሣራ፣ በዚያው በያዙት ተስፋ ቃል፣ በብዛታቸው እንደ ሰማይ ኮከብ እንደማይቈጠርም በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ የሆኑ ልጆች መባዛት ቀጠሉ!

ወገኖች ሆይ፣ ተስፋ ቃል ካለን፣ ጌታ ከተናገረን ጊዜው ቢሄድም፣ ጉዳዩ የቀረ ቢመስልም፣ ጊዜውን ጠብቆ መፈጸሙ አይቀርም! ተስፋ የሰጠው የታመነ ነውና፣ የተሰጠን ተስፋ ቃል ይፈጸማል እንጂ መሬት ላይ አይወድቅም! እግዚአብሔርም እንደ ተናገረው ያስበናልና፣ እንደ ተናገረው ያደርግልናል፣ ኃይልን በእምነት ልናገኝ ይገባል፡፡ ለእምነት ኃይል ተሐድሶ በመንፈስ ቅዱስ ሙላት መደገፍ ይገባል!

ወገኖች ሆይ፣ ኃይልን በእምነት በማግኘታቸው ምክንያት የሞቱ ከሚመስሉ ሰዎች፣ በብዛታቸው እንደ ሰማይ ኮከብ እንደማይቈጠርም በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ የሆኑ ልጆች ከተወለዱ፣ የሞትን ከማንመስል ከእኛስ እንዴት ያለ ሥራ ይከናወን ይሆን?

ወገኖች ሆይ፣ ኃይልን በእምነት በማግኘታቸው ምክንያት አብርሃምና ሣራ በዕድሜአቸው ሸምግለው ፈጽመው አርጅተው ሳሉ የተሰጣቸውን ተስፋ ቃል ካገኙ፣ እንደ እነርሱ በዕድሜ ያላረጀንና ያልገረጀፍን ሰዎች እንዴት ያለ ነገር እንቀበል ይሆን?

--------------------------------
‹‹የወንጌላዊ እጮኛ›› የተሰኘውና በሺዎች የተደነቀው ልብ አንጠልጣይ መጽሐፍ ታህሳስ 19 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ በ9፡00 ይመረቃል፡፡ ካዛንቺስ ኡራኤል መካነየሱስ አጠገብ በሚገኘው የኢትዮጵያ ሕይወት ብርሃን ቤተክርስቲያን ዋና ጽ/ቤት እንዲገኙልኝና ይህንን ታሪካዊ መጽሐፍ እንዲመርቁልኝ በአክብሮት ተጋብዘዋል፡፡


እምቢ በል!

ዲቮሽን .98/07     ረቡዕ ታህሳስ 8/07 ..
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


እምቢ በል!

ሙሴ ካደገ በኋላ የፈርዖን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ፤ ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና (ዕብ 11፡24-26)።

መወለድ ቋንቋ ነውና የትም ልንወለድ እንችላለን፡፡ ማደግም ዕድል ነውና የትም ልናድግ እንችላለን! ነገር ግን የሰው ልጆች ሕይወት ዋናው የጨዋታ ክፍል የሚጀምረው ካደጉ በኋላ ነው፡፡ ልማትም ሆነ ጥፋት ሥራ የሚጀምረው ዕድገት ሲመጣ ነው!

ወገኖች ሆይ፣ ሙሴ ካደገ በኋላ የፈርዖን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ፡፡ ይህ ውሳኔው በሰው እይታ ስህተት፣ በእምነት ሲታይ ግን ትክክል ነበር!

ታውቃላችሁ፣ አንዳንዴ በልጅነታችን የሚጣበቀብንን ጭቃ ማስለቀቅ አስቸጋሪ ነው! እግዚአብሔር ካልረዳ በስተቀር፣ ከልጅነት የሚወረስ ልማድ እንደ ሽንፍላ ሲታጠብም ቢውል ቶሎ የማይለቅቅ ነው!

ወገኖች ሆይ፣ ሙሴ ካደገ በኋላ የንጉሡን ቁጣ ሳይፈራ፣ ግብጽን የተወው በእምነት ነው! አንዳንዴ እግዚአብሔር ከማይከብርበት ሕይወት ጥሰን ለመውጣት ስንሞክር ተግዳሮት ይበዛል፡፡ ጨክነን ስንወጣ ደግሞ በውሳኔያችን የሚከፉ፣ አቋማችንን የማይደግፉ ገዥዎቻችን አሉ፡፡

ወገኖች ሆይ፣ ሙሴ በአቋሙ መጽናት የቻለው ‹‹የማይታየውን እንደሚያየው አድርጎ ስለ ጸና›› ነው። ወገኖች ሆይ፣ የዕብራዊያን ጸሐፊ ጮኾ የሚሰብከው ይህንን እውነት ነው!

ታውቃላችሁ፣ ሙሴ አሽንቀጥሮ የጣለው ሀብትና ማዕረግን፣ ዝናንና ክብርን ብቻ ሳይሆ የሀገር ንጉሥነትን ነው፡፡ ከግብፅ ንጉሥነት ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍን፣ ከግብፅ ብዙ ገንዘብ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ብዙ መከራ መቀበልን ነው! በኃጢአት ከሚገኝ ጊዜያዊ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ሐዘን መሸከምን ነው!  

ወገኖች ሆይ፣ የእግዚአብሔር ሰው ከጊዜያዊ ደስታ ይልቅ የሚዘልቀውን ሐሴት ይመርጣል! ከምድራዊ ሀብት ይልቅ ሰማያዊ ባለ ጠግነትን ያስባል! ከዛሬው ሁኔታ ይልቅ የወደፊቱን ብድራት ትኵር ብሎ ይመለከታል!

ታውቃላችሁ፣  ዛሬ ላይ ቆመን የእምነት መነጽር አድርገ የወደፊታችንን ስናይ፣ የሚጠብቀን ክብር፣ ከዛሬው ደስታ ይልቅ እጅግ የላቀ ነው! ለእርሱ ክብር ብለን በኃጢአት የሚገኘውን እምቢ በምንለው ፈንታ የተዘጋጀልን ብድራት እጅግ የላቀ ነው! ሙሴም ትኩር ብሎ ያየው ይህንን እውት ነው!

ወገኖች ሆይ፣ ሙሴ ካደገ በኋላ ስሙ በፈርዖን ልጅነት፣ በግብጽ ዜግነት እንዳይጠራ በእምነት እምቢ አለ! ታውቃላችሁ፣ ስማችንን በክፉ የሚያስጠራን ነገር እምቢ ልንል ይገባል! ስማችንን ከሚያቆሽሽ፣ ምስክርነታችንን ከሚያበላሽ ከማናቸውም ነገር ልንወጣ ይገባል፡፡

ወገኖች ሆይ፣ ማንነታችንን ጥለን፣ ሕይወታችን ጥለን፣ ጽድቅ ቅድስናችንን ጥለን፣ ክብራችንን ጥለን የምናገኘውን ማናቸውንም ደስታ እምቢ ልንል ይገባል! ከባርነት ምድር፣ ጌታ ከማይከብርበት ነገር፣ በኃጢአት ከሚገኝ ዝና፣ ሀብትና ክብር፣ በእምነት ለቅቀን እንውጣ!

--------------------------------

(ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክና ሼር ያድርጉ፣ ወዳጅ ጓደኞችም እንዲያገኙ ያግዙ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!)