Wednesday, July 22, 2015

ሰላምን ያደርጋል!!!!!

ዲቮሽን 311/07፥ ቅዳሜ፥ ሐምሌ 11/07 ዓ/ም
(በእህት ማርታ ሲሳይነህ)

ሰላምን ያደርጋል!!!!!

የሰው አካሔድ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ እንደሆነ፣ በእርሱና በጠላቶቹ መካከል ስንኳ ሰላምን ያደርጋል። ምሳሌ 16፡7
አንዳንድ ጊዜ በሕይወት መንገድ ላይ በብዙ ጉዳዮች ተጠምደን እንውላለን። በዚህ በማሕበራዊ መስተጋብራችን ውስጥም የተለያዩ ዓይነት ሰዎች ያጋጥሙናል። የሚወዱን፣ የሚጠሉን፣ ሐሳባችንን የሚደግፉ፣ ሐሳባችንን የሚቃወሙ፣ በገንዘም ሆነ በምክር የሚረዱን ወይም ደግሞ ያለንንም ነገር ቢሆን የሚወስዱብን፣ ልባችን የሚያርፋባቸው፣ ወይም በነገር እና በሐሜት ልባችንን የሚያደሙ .... ብቻ እጅግ በርካታ አይነት ሰዎች ይገጥሙናል።

በዚህ ጋጋታ ውስጥም ይህ አመጸኛ ስጋችን አንዳንዴ በስሜታዊነት ጎል ያስገባንና ለሰዎች መጫወቻ እንሆናለን። ጉዳይ ልናስፈጽም ብንል እየተሳደብን፣ መልእክት እናድርስ ብንል እየተቆጣን፣ ብቻ ግራ ያጋባናል-ይህ ስጋችን። ያን ጊዜ፣ ሰዎች እንኳን ሊታገሱን እስከማይችሉ ድረስ ይጸየፉናል፣ ወይም ደግሞ ይጠሙብናል። ክብር ለመንፈስቅዱስ ይሁንና፣ ወጀቡም ማእበሉም ሲያንገላታን አጽናኛችን አይጥለንም፤ ወደ ቃሉ ይመልሰናል።

ከዚያም በሁሉ ሙሉ የሆነው ንጹህ የእግዚአብሔር ቃል ይመክረናል፤ እንዲህ ሲል፣“ የሰው አካሔድ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ እንደሆነ፣ በእርሱና በጠላቶቹ መካከል እንኳን ሰላምን ያደርጋል”። ምሳሌ 16፡7

እንዲህ ያለ ነገር ገጥሟችሁ ያውቅ እንደሆነ ግዴላችሁም ወደ ቃሉ ተመለሱ። ጌታ ለዘላለም ስለማይጥለን ከእሱ ጋ እንስማማ፣ ደስ የሚያሰኘውንም እንፈልግ፣ ያን ጊዜ ብልሽትሽቱ የወጣው ማሕበራዊ ሕይወታችን፣ የሥራ ሁኔታችን፣ የጠሉን ሰዎች ሁሉ በስምምነት ከእኛ ጋር መኖርና መስራትን ይፈቅዳሉ።

ባባዬ፣ ደግ ነህና እወድሀለሁ። ደግ ስለሆነው ቃልህም ተባረክልኝ። ቁጥር ስፍር ስለሌለው ምክርህም አመሰግንሀለሁ። ሰምተህኛልና ተባረክ።
--------
ዕለታዊ ዲቮሽኑ ጳጉሜ 6/07 ዓ/ም ይጠናቀቃል፡፡ አሁን 55
ቀን ቀርቶታል፡፡

No comments:

Post a Comment