Wednesday, July 22, 2015

አንድም አልጠፋብኝም!!!!

ዲቮሽን 314/07፥ ማክሰኞ፥ ሐምሌ 14/07 ዓ/ም
(በእህት ማርታ ሲሳይነህ)

አንድም አልጠፋብኝም!!!!

ከሰጠኸኝ ከእነዚህ አንድም አልጠፋብኝም። ዮሐ 18፡9

ጌታን ካገኘን ጀምሮ እግዚአብሔር ወደ ሕይወታችን ያመጣቸው እጅግ ዓይነት በርካታ ሰዎች ይኖራሉ። የኛ ሕይወት አመቺም በሆነ መንገድ ይለፍም አይለፍም፣ የኛ ጸሎት ይመለስም አይመለስም፣ ክርስቲያን በመሆናችን ብቻ አምነውን ለእርዳታ ወደ እኛ የመጡ ብዙ ወንዶችና ሴቶች፣ ታናናሾች እና ታላላቆች ይኖራሉ።

ምክራችንን፣ ጸሎታችንን፣ ገንዘባችንን፣ እንክብካቤያችንን፣ ጊዜያችንን .... ፈልገው “እሱ አለ/እሷ አለች” ብለው የፈለጉንን ሰዎች የት አድርሰናቸው ይሆን? የክርስትና ሕይወት አቀበት ሲሆንብን መንገድ ላይ ጥለናቸው ይሆን?
ሲርበን፣ ሲጠማን፣ ስንታረዝ፣ በሕይወታችን ላይ ሰልፍ ሲበዛብን የራሳችሁ ጉዳይ ብለን አባረናቸው ይሆን?

እግዚአብሔርስ እነዚያን ሰዎች ያለነገር ወደ ሕይወታችን ዝምብለው ያመጣቸው ይመስላችኋል? ከፍቷቸው፣ ሆድ-ብሷቸው፣ ማልቀስ አምሯቸው እኛን ከሰው ሁሉ መርጠው የተጠጉንን ሰዎች የት አድርሰናቸው ይሆን?

እግዚአብሔር ሌላ ወገን ሰጣቸው ይሆን? ወይስ የሚያነሳቸው ጠፍቶ ተንከራተው ቀርተው ወይም ሞተው ይሆን? ምናልባት ጌታስ ድንገት ቢጠይቀን፣ እንደ ኢየሱስ፣ “ከሰጠኸኝ ከእነዚህ አንድም አልጠፋብኝም” ዮሐንስ ወንጌል 18፡9 የማለት ኃይል ይኖረን ይሆን? መልሱን ለእያንዳንዳችሁ ልተወው። ዛሬም ሌላ ቀን ነውና፣ ግን ካሁን በኋላ ልብ እንበል።

አባት ሆይ፣ በአንድም በሌላም ምክንያት ወደእኛ ያመጣሀቸውን ሰዎች አባርረናቸው እንደሆነ፣ ወይም በራሳችን ጉዳይ ተጠምደን፣ የነፍሳትን ነገር ችላ ብለን እንደሆነ፣ ወይም ስልካችንን እያጠፋን፣ በመንገድም አይተን እንዳላየን አልፈናቸው እንደሆነ፣ በውጤቱም የእነዚያ ሰዎች ሕይወት ተበላሽቶ እንደሆነ፣ ዛሬ እለምንሀለሁ፣ እኛንም ይቅር በለን፤ እነሱንም ከወደቁበት የሚያነሳውን መንፈስህን ላክላቸው። ሰምተህኛልና ተባረክ።
--------
ዕለታዊ ዲቮሽኑ ጳጉሜ 6/07 ዓ/ም ይጠናቀቃል፡፡ አሁን 52 ቀን ቀርቶታል፡፡

No comments:

Post a Comment