Wednesday, July 22, 2015

ባለስልጣን!!!!

ዲቮሽን 313/07፥ ሰኞ፥ ሐምሌ 13/07 ዓ/ም
(በእህት ማርታ ሲሳይነህ)

ባለስልጣን!!!!

ስልጣን ከሰማያት እንደሆነ ካወቅህ በኋላ መንግሥትህ ይቆይልሃል። ዳንኤል 4፡27

የመጨረሻው ዘመን አሠራር እጅግ በረቀቀ እና በተወሳሰበ ስልት ሕይወታችን እያመሰ ያለበት ወቅት ላይ ነን። አማኝ ነን ለምንል ለእኛም ቋንቋችንን እየደበላለቀ፣ እርስ በርሳችን ለእግዚአብሔር ቤት ሥራ እንዳንተጋ ያደረገበት ወቅት ነው።

በሚያልፍና በሚጠፋ ነገር ውስጥ ተተብትበን፣ የክርስቶስን ሰላም እንደ ቀላል ያቃላለንበት ወቅት ነው አሁን። አንዳንዴ ራሳችን ለራሳችን ምን ነክቶኝ ነው እንዲህ የሆንኩት? እስክንል ድረስ በማይገባን ሥፍራ፣ የማይመጥነን ስራና አመል እያሳየን፣ ትእግስት እየጎደለን፣ ስንባዛን ራሳችንን እናገኘዋለን።

በቤተክርስትያንም ያለው አሠራር ደስ የሚያሰኘውንም ያህል፣ ልብን የሚያዝል ነገር አለው። አልፎተርፎም እግዚአብሔር አለ ወይስ የለም? በዚህ ጊዜ ምን እየተከናወነ ነው? ለኔስ ሆነ ለቀሪው ቤተሰቤ፣ ለራእየና ለሀገሬ ምን ተስፋ አላት? እያልን በተስፋ መቁረጥ ውስጥ የምንመላለስበት ሰዓት ነው አሁን። አንድ ነገር እነግራችኋለሁ፣ እግዚአብሔር አለ። እየሆነ ያለውንም ነገር ሁሉ ያውቀዋል። የተበላሸ የቤተክርስትያናችንንም ሆነ የሕይወታችንን ክፍል ያውቀዋል። መፍትሔ ፍለጋም ወደቀኝ እና ወደግራ ስንባክንም ያውቀዋል። የጨለማው ገዢ በመጨረሻው ሰዓት ትንቅንቅ ላይ ስለሆነ ራሳችሁን ባልተገባ ቦታ ላይ ብታገኙት አይግረማችሁ።

ስልጣን ያለው በሰማይ ነው። የሰማይና የምድር ፈጣሪ አንድ እግዚአብሔር ይደርስልናል። እኛ ብቻ በድካምም ውስጥ ብንሆን፣ አባት ሆይ እባክህ ዓይኖቼን ክፈት እያልን እንጸልይ። ወደ ቀኝ ወደ ኋላ ማለታችንንም ትተን ወደሰማይ ብቻ እንመልከት። እጅ እንስጥ። መፍትሔ ያለው ከሰማይ ነው። መላ ያለው ከአብ ዘንድ ነው። ከሌላ ከየትም የለም። እኛ ስልጣን ከሰማይ መሆኑን እንወቅ እንጅ፣ እኛ እግዚአብሔርን እንፈልገው እንጠጋጋው እንጅ፣ እንጠጋጋው እንጅ፣ ያን ጊዜ የተዝረከረከው ነገር ሁሉ ቦታ ቦታውን በራሱ ጊዜ ይይዛል።

አባት ሆይ፣ ግሩም መካሪ ስለሆንክልን ተባረክ። ወዳጅ ሆይ ስምህ ለዘላለም ይባረክ። መንፈስቅዱስ ሆይ፣ ባስጨነቁን ላይ በእሳት ስለምትገለጥ ተባረክ። ሰምተህኛልና ተባረክ።
--------
ዕለታዊ ዲቮሽኑ ጳጉሜ 6/07 ዓ/ም ይጠናቀቃል፡፡ አሁን 53 ቀን ቀርቶታል፡፡

No comments:

Post a Comment