Wednesday, July 22, 2015

አወሩ!!!!!

ዲቮሽን 312/07፥ እሁድ፥ ሐምሌ 12/07 ዓ/ም
(በእህት ማርታ ሲሳይነህ)

አወሩ!!!!!

እግዚአብሔርም ከእነርሱ ጋር ያደረገውን ሁሉ አወሩ። ሐዋ 15፡ 4

በዘመናችን ጌታ ያደረገልን ነገር ብዙ ነው። ጠላቶቹ ስንሆን ወዳጅ አድርጎን፣ ውሸተኛ ስንሆን በልጁ በኢየሱስ እውነት ሸፍኖን፣ በሽተኞች ስንሆን በመገረፉ ቁስል ፈውሶን፣ ከርታቶች ስንሆን በእቅፎቹ ይዞን፣ የማንመች ለሆንነው ለኛ፣ የሚመች ሆኖ፣ ለሚቆረቁረው ማንነታችን የማይቆረቁር ስሙን ሰጥቶን፣ ሌቦች፣ ዘማውያን፣ ተሳዳቢዎች ስንሆን... ተሸክሞን ይኼው አለን።

እስከዛሬ ድረስ፣ እሳከሁኗ ደቂቃ ድረስ፣ ያለነው ጌታ ተጠንቅቆልን ነው። መንገድ የጠፋን ቅብዝብዞች ሆነን እያለ፣ መንገድ ሆኖልን። በምድረበዳው፣ በሐሩር እና በቁሩ፣ በዳገት እና ቁልቁለቱ፣ ሰለቸኝ ደከመኝ ሳይል፣ እዚህ ያረሰን እግዚአብሔር ነው። ጠላት ሊያበራየን ሲመጣ፣ ጌታ ከልክሎልን እስካሁኗ ሰከንድ ድረስ አለን።

ታዲያ ዛሬ ለገጠመን ነገር እንዴት እንዴት ምንም እንዳልተደረገለት ሰው ጨለማ ይውጠናል? ታዲያ ዛሬ ላላንበት ነገር እንዴት ልባችን ይዝላል? በጉልበታችን፣ በእውቀታችን፣ በገንዘባችን አልኖርንም አይደል? ስለዚህ፣ አይዞን፣ አይዟችሁ። ድብርት፣ ተስፋ መቁረጥና፣ አዚም ሲጫጫናችሁ/ ሲጫጫነን እንዲህ አድርጉ። እግዚአብሔር በሕይወታችሁ ላይ ያደረገላችሁን ነገር ተጨዋወቱት።

ብቸኝነት ይዟችሁ፣ የምታካፍሉት ሰው ከሌላችሁ እንኳን፣ ወደ ሰማይ ቀና ብላችሁ አሰላስሉት። አስቡት። ለልቦናችሁ ንገሩት። እርግጠኛ ሆኜ የምነግራችሁ፣ ያ የምሕረት አምላክ አላረጀም፣ አልደከመም፣ አልሰለቸም። በደጅ ነው። በርቱ።
አባት ሆይ፣ ስለሰማህኝ አመሰግንሀለሁ። በእርግጥ ያደረክልን ነገር ብዙ ነውና እሱኑ እንድንጨዋወተው እንድናሰላስለው ስለመከርከን ተባረክ። ሰምተህኛልና ተባረክ።
--------
ዕለታዊ ዲቮሽኑ ጳጉሜ 6/07 ዓ/ም ይጠናቀቃል፡፡ አሁን 54 ቀን ቀርቶታል፡፡

No comments:

Post a Comment