Sunday, February 15, 2015

እንቁልልጭ ቢበዛም!

ዲቮሽን ቁ.155/07፣ ሐሙስ፥ የካቲት 5/07 ዓ.ም.
(በማርታ ሲሳይነህ)

እንቁልልጭ ቢበዛም!

“እስማኤልን ብቻ ባርከህ ባኖርክልኝ” (ዘፍ 17፡18)
ይህንን ያለው፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ፣ ወይም ጓደኛ ሆኖ ሳለ፣ የተስፋው ቃል “ላም አለኝ በሰማይ” የሆነበት፣ ሽማግሌው አብርሐም ነው። ሁልጊዜም፣ አብርሐምንና እግዚአብሔርን ሳስባቸው በፊቴ መጥቶ ድቅን የሚልብኝ ጥብቅ ጓደኝነታቸው ነው። አብርሐም፣ ዘፍ 12፡7 ላይ “ታላቅ ህዝብ አደርግሐለሁ” ያለውን አንድ እግዚአብሔርን አምኖ፣ ከሥጋ ዘመዶቹና ወገኖቹ ተነጥሎ በ75 ዓመቱ ወጣ።
ከዘመድ እና ከወዳጅ፣ መለየትን መቼም የደረሰበት ሰው ያውቀዋል! እንደገና በ12፡7 ላይ፣ “ይሕችን ምድር ለዘርህ እሰጣለሁ” ብሎ ወዳጁ እግዚአብሔር ቃል ገባለት። ቢሆንም ግን፣ ከጥጋብ የወጣው አብርሐም፣ ጭራሽ ተራበ (12፡10)፣ ይህም አለፈና፣ እግዚአብሔር አሁንም “ዘርህን እንደ ምድር ትቢያ አበዛዋለሁ” አለው (13፡16)። ቀጥሎም፣ “ከአብራክህ የሚከፈል ልጅ ወራሽህ ይሆናል” አለው (15፡5)።
ይሕ ሁሉ ሲሆን፣ ለአብርሐም፣ የልጅ ጉዳይ የሁልጊዜ ጥያቄው እንደሆነበት አለ። አንድ ልጅ ‘የሕልም እንጀራ’ ለሆነበት ለአብርሐም፣ እግዚአብሔር ግን፣ ምን ገዶት? የትውልዱን ራዕይ አሳየውና፣ “በአራተኛው ትውልድ ዘርህ ወደዚህ ምድር ይመለሳል” አለው(15፡16) ። አብርሐም ይህን ጊዜ በልቡ፣ ‘ወይ አንተ! ትቀልዳለህ? እኔ አንድ ልጅ እንዳማረኝ ልሞት ነው፣ አንተ ስለ አራተኛ ትውልድ ትናገራለህ? ምናለበት ዝም ብትል?’ የሚል ይመስለኛል።
በመጨረሻም፣ 11 ዓመት ሙሉ የልጅ ጠኔ ለያዘው ለአብርሐም፣ በሳራ በኩል ዘዴ ተዘየደለትና፣ ከአጋር በ86 ዓመቱ እስማኤልን አገኘ። “እንዲያው እስከ ዛሬ ድረስ ይህን ማድረግ ስችል፣ እግዚአብሔርን አጉል ስጠብቅ 11 ዓመታትን አቃጠልኩ፤ እስከዛሬ እኮ የዓሥር ዓመት ልጅ አደርስ ነበር! ምንኛ ሞኝ ሰው ነኝ!” ያለ ይመስለኛል።
እስማኤል፣ ወደ 13 ዓመት ሲሆነው፣ አሁንም እግዚአብሔር፣ ምን ተስኖት? (17፡1-14) ላይ፣ “ዘርህን አበዛለሁ” እያለ፣ ሰፋ ያለ የትውልድና የግዝረትን ኪዳን ይናገረዋል። አሁን፣ የ99 ዓመቱ አብርሐም፣ አባት ስለሆነ፣ ደረቱን ነፋ፣ አድርጐ፣ እግዚአብሔር ከመጀመሪያ ጀምሮ እስካሁን የገባለትን ኪዳን፣ በልዩ ብርታት እያስታወሰ፣ በእጁ የያዘውን እስማኤልን እያሰበ፣ ወዳጁ እግዚአብሔርን ያደምጠዋል።
ጉድ የፈላው 17፡15 ላይ፣ የቃልኪዳን ልጁ፣ ከሣራ እንደሚወለድ ሲነግረው ነው። ይህን ጊዜ፣ አብርሐም፣ እንደመከፋት ያለ ሳቅ ሳቀና፡- እንዲያው፣ ቀልዱን ተወውና፣ “እስማኤልን ብቻ ባርከህ ባኖርክልኝ!” ዘፍ 17፡18 ይለዋል። ጐመን በጤና ዓይነት ንግግር ነው! ሆኖም፣ ምን ተስኖት፣ የሆነው እግዚአብሔር፣ በ90 ዓመቷ ሣራን አሰባትና፤ ከ25 ዓመታት በኋላ፣ አብርሐም፣ በመቶ ዓመቱ ይስሐቅን አገኘ። የተስፋው ቃልም ተፈጸመ።
ዛሬም፣ እግዚአብሔርን፣ በልዩ ልዩ ሁኔታ ለጠበቅነው፣ ከተስፋ ቃላችን መዘግየት የተነሳም፣ ተስፋ ቆርጠን፣ መልካም አማራጭ የመሰለንን እስማኤልን ለያዝን፣ እግዚአብሔርንም፣ “ሌላው ሌላው ሁሉ ቀርቶብኝ፣ እንቁልልጭ ያልከኝ ነገር ሁሉ ቀርቶብኝ፣ እስማኤልን ብቻ ባርከህ ባኖርክልኝ”፣ ለምንለው፣ ለእያንዳንዳችን፣ በእርግጥ፣ ይስሐቅ ይወለዳል፤ ኤፌ 3፣20 “ከምንለንምነው ወይም ከምናስበው ሁሉ በላይ እጅግ አብልጦ ማድረግ ለሚቻለው”፣ ለእግዚአብሔር፣ ምንም የሚያቅተው ነገር የለምና”!!!!!!
----
ትምህርቱ ጠቅሞዎታል? እንግዲያውስ ሼር እና ላይክ ያድርጉ ፤ ጌታ ይባርክዎ!
- - - - - -
የወንጌላዊው እጮኛ አዲስ መጽሐፍ በገበያ ላይ ውሏል ። ለተጨማሪ መረጃ በ0911 678158 ወይም በ0911 803092

No comments:

Post a Comment