ዲቮሽን ቁጥር 156/07፣ አርብ፣ የካቲት 6/07
(በማርታ ሲሳይነህ)
“እባክህን፣ የአኪጦፌልን ምክር ወደ ከንቱነት ለውጠው?” 2ኛ ሳሙ፡15፡ 31
ይህንን ጸሎት ያደረገው፣ እግዚአብሔር እንደ ልቤ ያለው ንጉሥ ዳዊት ነው። ንጉሥ ዳዊት እግዚአብሔር ምን እንደሆነ፣ ማን እንደሆነ፣ የኃይሉንም ሆነ የቁጣውንም ጥግ፣ እንዲሁም የሥልጣኑን የበላይነት፣ የማያቋርጥ ምሕረቱንና ፍቅሩን ከልጅነቱ ጥንቅቅ አድርጎ በማወቁም፣ በመዝ 111፡ 10 “የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው” በማለት ይናገራል። እስከመጨረሻውም ድረስ፣ ጠላቶቹን ሁሉ ያሸነፈው በዚሁ መርሁ ነው። “ዕድሜም፣ ባለጠግነትንም፣ ክብርንም ጠግቦ በመልካም ሽምግልና ሞተ” 1ኛ ዜና፣ 29፡ 28፣ ተብሎ እስከተነገረለት ድረስ፣ ይህንን ፍርሐት ጠብቆ፣ ተግብሮም አሳይቶናል።
ዓመጸኛው አቤሴሎም፣ እንደ አባቱ ብርቱ ጦረኛ እና ብልሕም ነበር። ብልሕ በመሆኑም ነው፣ 2ሳሙ 15፡8 “ወደ ኬብሮን ለእግዚአብሔር እሰግዳለሁ” ብሎ አባቱን ዋሽቶት በሚሔድበት ጊዜ፣ አኪጦፌልን ይዞት የሔደው። የዳዊት አማካሪ የነበረው “አኪጦፌል፣ የሚሰጠው ምክር የእግዚአብሔርን ቃል እንደ መጠየቅ ይቆጠር ነበር፤ ዳዊትም ሆነ አቤሴሎም የአኪጦፌልን ምክር የሚቀበሉት በዚህ ሁኔታ ነበር” 2ሳሙ16፡23።
አኪጦፌል፣ የተናገረው ሁሉ ከመሬት ጠብ የማይል፣ በምክር ግሩም የሆነ፣ ኃያል ጦረኛ ነው። አቤሴሎምንም፣ “ኣባትህ ከተዋቸው ቁባቶቹ ጋር ግባና ተኛ፣ ከዚያም አንተ አባትህን እጅግ የጠላህ መሆንህን መላው እስራኤል ይሰማና አብሮህ ያለው ሁሉ ክንዱ ይበረታል” 2ሳሙ 16፡ 21-22 ብሎ፣ ከሰው ልማድ ውጭ የሆነውን ድርጊት መላው እስራኤል እያየው፣ ከአባቱ ቁባቶች ጋር በጠራራ ጸሐይ፣ እንዲተኛ ያደረገው ሰው ነው።
ዳዊት፣ አቤሴሎምን ሸሽቶ፣ እያለቀሰ፣ በባዶ እግሩ የደብረ ዘይትን ተራራ እየወጣ ሳለ፣ “ከአቤሴሎም ካሴሩት መካከል አንዱ አኪጦፌል ነው” የሚል መረጃ ደረሰው። ያ፣ የእግዚአብሔርን ልዕለ-ኃያልነት እና ወሰን የለሽ የማድረግ ብቃት፣ የሚያውቀው ዳዊት ግን፣ እያለቀሰም፣ እንባውን መንታ፣ መንታ አድርጎ እያወረደም፣ ዙፋኑን ጥሎ እየሸሸም፣ ቢሆን፣ በእግዚአብሔር መደገፉን አላቋረጠም፤ “እግዚአብሔር ሆይ፣ እባክህን፣ የአኪጦፌልን ምክር ወደ ከንቱነት ለውጠው” 2ኛ ሳሙ፡15፡ 31 በማለት እግዚአብሔርን ተማጸነ። እግዚአብሔርም፣ በምዕ. 17 ላይ እንደምናየው፣ የአኪጦፌልን ምክር መና አደረገው። በሕይወት ዘመኑ ለመጀመሪያ ጊዜ፣ ምክሩ ተቀባይነት ሳያገኝ የቀረው አኪጦፌልም፣ አንድም ስለተናቀ፣ አንድም፣ ዳዊት እንደሚያሸንፍ በማወቁ እና የሚከተለውን መዘዝ በማወቁ፣ 17፡23 ላይ በገዛ እጁ ታንቆ ሞተ።
ዛሬ፣ የእኔና የእናንተ አኪጦፌል ማነው? ምንድነው? እውነት የሆነ፣ እውነትነቱ ግን፣ ግን በእኔና በእናንተ ላይ፣ ውርደትን፣ ሽንፈትን፣ ኃዘንን፣ የማያባራ ለቅሶን፣ የሚያስከትል፣ አኪጦፌሊያዊ ምክር ምንድነው? እውነት ከመሆኑ የተነሳ፣ “በኔና በሞት መካከል አንድ እርምጃ ብቻ ቀረ” ያስባለን (1ኛ ሳሙ 20፡2)፣ እውነት ከመሆኑ የተነሳ፣ “ልቤ በላዬ ተናወጠብኝ፣ የሞት ድንጋጤም ወደቀብኝ፣ ፍርሀትና እንቅጥቅጥ መጡብኝ፣ ጨለማም ሸፈነኝ፣ በርሬ ዐርፍ ዘንድ እንደ ርግብ ክንፍን ማን በሰጠኝ”፣ መዝ 55፡ 4-6 ያስባለን፣ አኪጦፌላችን ምንድነው?
እጸልያለሁ፤ አብ አባት ሆይ፣ “እግዚአብሔር በሚፈሩት፣ በምሕረቱ በሚታመኑትም ይደሰታል” መዝ 147፡11 ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ እኔና ሕዝብህን፣ ሊያዋርድና ሊያጠፋ፣ የተሸረበ ማንኛውም አኪጦፌሊያዊ ምክር ሁሉ፣ ዛሬ፣ አሁን፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከንቱ ይሁን!!!!!!! አሜን
------
ትምህርቱ ጠቅሞዎታል? እንግዲያውስ ሼር እና ላይክ ያድርጉ፤ ጌታ ይባርክዎ!
----------------
‘የወንጌላዊው እጮኛ’ አዲስ መጽሐፍ በገበያ ላይ ውሏል። ለተጨማሪ መረጃ በ ወይም በ ይደውሉ።
No comments:
Post a Comment