ዲቮሽን 262/07፥ ቅዳሜ፣ ግንቦት 22/07
(በዶ/ር በቀለ ብርሃኑ)
(በዶ/ር በቀለ ብርሃኑ)
የማይወሰድ ዕድል
የጸጋው ዙፋን የምሕረት፣ የሕክምናና የፈውስ ቦታ ነው፡፡ የሚገርመው ነገር ግን ወደዚህ የፈውስ ማዕከል እንዳንመጣና እንዳንፈወስ፣
እንዳንለወጥና ለሌሎች በረከት እንድንሆን የማይመጣ የተግዳሮት ዓይነት የለም፡፡
ሁሌ የሚገርመኝ ነገር አለ፡፡
የጨለማው ዓለምና አጋንንቱ ሌሎችን ተግባራት ስናከናውን ምንም ግድ አይሰጣቸውም፡፡
ወደዚህ የፈውስ ቦታ ለመምጣት ስናስብ ግን አዚማቸውንና ተቃውሞአቸውን በተለያየ መንገድ ይገልጻሉ፡፡ ወስነን ለጸሎትና ከጌታ ጋር በተለያየ መንገድ ሕብረት ለማድረግ ስንነሣሣ፣
ስልቹ ሆነን እንድናቋርጥ፣
ቶሎ ጨርሰን ወደ ሌላ ጉዳዮች እንድንሄድ ጫናቸውን ይጨምራሉ፡፡ የጸሎትን ጥቅም ማሣነስም ትልቅ መዋጊያ መሣሪያቸው ነው፡፡
በግል ሕይወቴና ከጌታ ጋር በርከት ያለ ጊዜን ከሚያሳልፉ ሰዎች እንደተማርኩት፣ በጌታ እግር ሥር መሆን ብዙ ጥቅም አለው፡፡ ከሁሉ ሊተኮርበት የሚገባው ጥቅም ግን ውስጣችን መለወጡ ነው፡፡ ውስጣችን ዕለት ዕለት መታደሱ ነው (2ቆሮንቶስ 4፡16)፡፡ ልባችን የመንፈስ ፍሬዎችን ማፍለቁና መንፈሳችን መጠንከሩ ነው፡፡
ከላይ እንደጠቀስኩት ከጌታ ጋር በቂ ሕብረት እንዳይኖረን የማይመጣ የጠላት ተጽዕኖ የለም፡፡
ቢሆንም እነዚህንጫናዎች ተቋቁመን በሱ ፊት በቂ ጊዜን ብናሳልፍ፣
ሕይወታች በሚገርም ሁኔታ ይለወጣል፡፡ ያኔ አቅም ባጣንባቸው ነገሮች ላይ ጉልበት እናገኛለን፡፡
ያኔ “እምቢ” ማለት ባቃቱን ነገሮች ላይ የበላይ እንሆናለን፡፡
እውነተኛ መንፈሳዊ ለውጥና በረከት፣ የምር የሆነ መሻትን ይፈልጋል፤ ራብንና ጉጉትም ያስፈልገዋል፡፡ ይህንን ሐሳብ አስመልክቶ ኢየሱስ “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው ይጠግባሉና” ብሎ ድንቅ መንፈሳዊ መርሕን አብስሮናል፡፡ እኔ ሁልጊዜ “ይጠግባሉና” የሚለው ተስፋ በኃይል የሚያስደንቀኝና ጉጉትን የሚፈጥርብኝ፡፡
አዎ መንፈሳዊ ራባችንና ጥማታችን እያየለ ሲሄድ፣
አስደናቂ ሕይወት ውስጥ ራሳችንን እናገኘዋለን፡፡
እናም መሻታችን እየጨመረ ሲሄድ፣ ሌሎች ብዙ ረብ የሌላቸውን ነገሮች የመጣል ድፍረትን እናገኛለን፤ ምክንያቱም ነፍሳችን በጌታ እያረፈች ትመጣለችና ነው፡፡
ምክንያቱም ነፍሳችን ከተተበተበችበት የማይታዩ ሰንሰለቶች ነጻ ትሆናለችና ነው፡፡
የእግዚአብሔር ቃል “ዕረፉ እኔም አምላክ እንደ ሆንሁ እወቁ”(መዝሙር46፡10) ብሎ ይናገራል፡፡ ታዲያ “ዕረፉ” ማለቱ ጌታ አምነን፣ በፊቱ እየጸለይን፣ ቃሉን እየተመገብንና በእግሩ ሥር ሆነንና እሱን እየጠበቅን መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ኢየሱስ ስለዚህ ዕረፍት ሲናገር “ማርያም መልካም ዕድልን መርጣለች፣ ከርሷም አይወሰድባትም” (ሉቃስ 10፡42) ብሎ ተናግሯል፡፡ በርግጥም በሚገባ ከተዘወተረ የማይወሰድ ዕድል!
ጌታ ሆይ የጸሎትን መንፈስ አፍስስልን! እባክህ በፊትህ የመሆንን ዕድል አብዝተህ ስጠን! የጋለ ፍላጎትና መንፈሳዊ መሻትን በልባችን ላይ አፍስስ!
ትምህርቱ ጠቅሞዎታል? እንግዲያውስ እባክዎ ላይክና ሼር ያድርጉ፣ ጌታ ይባርክዎ።
No comments:
Post a Comment