Thursday, April 30, 2015

ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና - ዘመኑን ዋጁ !

ዲቮሽን 232/07 ሓሙስ ሚያዚያ 22/07
(
በወንድም ጌታሁን ሓለፎም)


ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና - ዘመኑን ዋጁ !

"እንግዲህ እንደ ጥበበኞች እንጂ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንዴት እንድትመላለሱ በጥንቃቄ ተጠበቁ ቀኖቹ ክፉዎች ናቸው እና ዘመኑን ዋጁ" (ኤፌ 5-15-17)

ቴክኖሎጂው በረቀቀበት በዚህ ዘመን፤ በአራቱም ማእዘን በተለያዩ ክፍለ አለማት የሚከናወነውን ድርጊት እና ሁኔታ አንድ ቦታ ላይ ሆኖ ለመከታተል እና ለማወቅ ከመቸውም ይልቅ እንደዚህ ዘመን ምቹ የሆነበት ወቅት የለም፡፡ ቴሌቪዥኑ፥ ጋዜጣው፥ እንተርኔቱ ሁሉ የአለምን ገጽታ ያለንበት ቦታ ድረስ ትኩስ ትኩሱን ይዞልን ይመጣልሳሎናችን ድረስ !

ታዲያ አይኖቻችን እና ጆሮቻችን ከመልካሙ ይልቅ ክፉውን፥ ከምስራቹ ይልቅ መርዶውን፥ ከደስታ ይልቅ ሓዘንን እና ድንጋጤን ጠግበው መሽቶ ይነጋል፡፡ ከዚህም ተጽኖ የተነሳ ነፍሳችን በፍርሃት እና በድንጋጤ ጫጭታለች፡፡ በሁሉም ሰው ፊት ተስፋ መቁረጥ ይነበባል፡፡

ዛሬ አለም በውጥረት ላይ እና በጭንቅ ውስጥ እንዳለች ለሁሉም ግልጽ ነው፡፡ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ምድርን እያናወጣት ነው፡፡ የመሬት መንቀጥቀጥ፥ የጎርፍ እና የእሳት ቃጠሎ በተከታታይ የተለያዩ ቦታዎችን እየመታ ነው፡፡ ጦርነት ድርቁ በሽታውና እርዛቱ ለጉድ ነው፡፡ 

ፍርሃት እና ድንጋጤ በየቦታው ወድቋል፡፡ ሁሉ ነገር የአለምን የከፋ ሁኔታ የሚያሳብቅ እንጅ የወደፊቱን መልካም ዘመን የሚጠቁም አይደለም፡፡

በሰዎች መካከል ፍቅር ጠፍቶአል፡፡ ወንድም ወንድሙን ይገድላል፥ አባት በልጅ ላይ ጨክኖአል፥ መንግስታት በመንግስታት ላይ ተነስተዋል፥ በሰዎች መካከል ስነ ምግባር ተበላሽቷል፥ ነውር እርቃኑን ወጥቶ አደባባይ ውሏል፡፡

ዘመኑ ክፉ ነው! ይህንን የተረዳው ጳውሎስ ለዚህ ነው እንግዲህ የዛሬ 2000 አመትገደማ በዘመኑ ለነበሩት ለኤፌሶን ቤተክርስቲያን ምእመን ሲጽፍ ቀኑ ክፉ ስለሆነ አትዘናጉ፥ እንደ እግዚአብሔር ሰው ጥበበኛ ሁኑ፡፡ ቀኑን ወቅቱን መርምሩ በዚህ በከፋ ዘመን እርኩሰት እና ክፋት በተንሰራፋበት ወቅት አካሄዳችሁ እርምጃችሁ የጥንቃቄ ይሁን፤ ዘመኑ እየከፋ፥ እየተበላሸ እንጅ መልካም ዘመን ይመጣል ብላችሁ አትጠብቁ፡፡ ከጌታ እና ከመንፈሱ ጋር ተጣበቁ፡፡

እውነት ነው ወገኖቼ፥ ከመቸውም ይልቅ ስለ ጽድቅ የሚሰበክበት ዘመን ቢኖር አሁን ነው፡፡ የዚህ ዘመን መሪ አገልግሎታችንም ቢሆን ሰዎችን ወደ ንስሃ መጥራት፥ ከሃጢያት እስራት በወንጌል ነጻ ማውጣት፤ በጾም በጾሎት በጌታ ፊት መቆየት ዋነኛ ተግባራችን መሆን አለበት፡፡

እያንዳንዱ ቀናችንን እንደዋጀን እርግጠኞች መሆን አለብን፡፡ የምትባክን በፌዝ እና በቧልት የምታልፍ ጊዜ ሊኖረን አያስፈልግም፡፡ ስለዚህ እናንተ የጌታ ብሩካን እንድንጸና እና እንድንጸልይ በመጠን እየኖርን፤ ለጌታ ክብር ጊዜውን እንዋጅ !

ትምህርቱ ጠቅምዎት ከሆነ፥ ላይክ ያድርጉ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!

No comments:

Post a Comment