Saturday, February 28, 2015

የጨለማ ሽንፈት!

ዲቮሽን .170/07፣ አርብ የካቲት 20/07 ..
(
በፓ/ር ተስፋሁን ሐጢያ)


የጨለማ ሽንፈት!

ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም (ዮሐ 15)

የብሉይ ኪዳኑ ነቢይ ኢሳይያስ (92) እንደተነበየው፥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህች ምድር ሲመጣ፥ "በጨለማ ይሄድ የነበረው ሕዝብ ብርሃን አየ፥ በሞት ጥላ አገርም ለሚኖሩ ብርሃን ወጣላቸው፡፡

ወገኖች ሆይ፥ ጌታችን ኢየሱስ ወደዚህ ምድር የመጣው መንፈሳዊ ብርሃን ሊሰጠን ነው፡፡ መንፈሳዊ ጭለማን ገፍፎ፥ መንፈሳዊ ብርሃን ሊሰጠን! ኦ፥ ሃሌሉያ! ጌታ ወደ ሕይወታችን የገባው ጨለማችንን ገፍፎ፥ በጨለማ ውስጥ ብርሃን ይሁን ሊል፥ የጨለማን ስራ ሊያፈርስ፥ በብርሃን እንድንመላለስ ነው!

ጌታን ስንቀበል ውጦን የነበረው ትብታብ፥ ጫካና አረንቋው፥ የአጋንንት ስንክሳር፥ ጥንቆላ መተቱ፥ አፍዝ አደንግዙ፥ በጌታ ኢየሱስ ብርሃን መታሰቢያው ጠፍቶ ነጻ እንድንወጣ ነው!
ታውቃላችሁ፥ ብርሀኑ በጨለማ ሲበራ ጨለማ አያሸንፈውምና፥ በዘር በግንዳችን፥ በደም በስጋችን፥ በአቻ ጋብቻችን የተጣበቀብን የጨለማ መንፈስ ድራሹ ይጠፋል! የአባት የአያታችን፥ ቅማያት ምንጅላት ምንትስ ያደረጉት ኪዳን፥ የፈጸሙት መሃላ፥ የቀረጹት ጣዖት፥ የተከሉት ሐውልት፥ ብትንትኑ ይወጣል!

ታውቃላችሁ፥ ጌታን ስንቀበል፥ የኢየሱስ ብርሃን በእኛ ላይ ሲበራ፥ "ወልጄ አሳድጌ፥ ወግ ማዕረግ አድርሼ፥ ለፍቻለሁና አልለቀውም እያለ የሚጎርር መንፈስ በዝረራ ይወድቃል! ሃሌሉያ!

ታውቃላችሁ፥ በሕይወታችን ላይ ብርሃን በርቷልና፥ አወቅን አላወቅን፥ ገባንም አልገባን፥ እኛን እንዲያጠፋ የተላከ መንፈስ፥ ጠንቋይ ሞራ ገላጭ፥ ሰላቢ ገጣቢ፥ ፈልፈላ ድግምቱን ኤልሻዳዩ ጌታ ከእግራችን በታች ጥሎ ይረግጠዋል!

ታውቃላችሁ፥ ብርሃኑ ሲበራ እርግማን ነጋሪ፥ ጨረር አስቀባሪ፥ ኮረኮንች ወርዋሪ፥ ኮከብ አስቆጣሪ፥ መድሀኒት ቀማሚ፥ ጥላ ወጊ መንፈስ በጌታ በኢየሱስ ተመትቶ ይወድቃል! በያዕቆብ ላይ አስማት፥ በእስራኤልም ላይ ሟርት የለምና፥ በእግዚአብሔር ሕዝብ ላይ የጨለማ ስራ በፍጹም አይሰራም!

ወገኖች ሆይ፥ የኢየሱስ ብርሃን በእኛ ላይ ከበራ፥ ተኛንም ተነሳን፥ ነቃንም አልነቃን፥ ሕዝቡን የሚጠብቅ አይተኛም፥ አያንቀላፋምና የጨለማ ስራ ሊያሰጋን አይችልም!


ታውቃላችሁ፥ ብርሃኑ በጨለማ ሲበራ፥ ጨለማ አያሽንፈውምና በዙሪያችን ያለ የትኛውም ጨለማ ይህን ብርሃን ማቆም፥ ኢየሱስን መቃወም፥ በጨለማው ግዛት ወንጌል እንዳይሰበክ፥ ምርኮ እንዳይማረክ ማገድ፥ መገዳደር በፍጹም አይችልም!

የጥበብና የመገለጥ መንፈስ!

ዲቮሽን .171/07፣ ቅዳሜ የካቲት 21/07 ..
(
በጌታሁን ሓለፎም)


የጥበብና የመገለጥ መንፈስ!

‹‹የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብን እና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ›› (ኤፌ 1:17)፡፡

ይህ መልእክት ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፈሶን ቤተክርስቲያን እና በዚያን ዘመን በአካባቢው ላሉ ምእመናን እየተዘዋወረ እንዲነበብ ታስቦ የጻፈው ደብዳቤ ነው:: ምእመኑ ዲያና (አርጠምስስ ) ትባል ከነበረች የጣኦት አምልኮ ፊቱን አዙሮ ክርስቶስን በማመን እና እርስ በርስ በመዋደድ ያሳየው እድገት መልካም ነበር፡፡ ይህ መልእክት እግዚአብሔር ምእመኑን ወደ በለጠ ከፍታ ይዞአቸው እንዲገባ የጸለየበት እና የቃተተበት መልእክት ነው::

እግዚአብሔርን በማወቅ የጥበብ እና የመገለጥ መንፈስ እንዲሰጣችሁ እጸልያለሁ፡፡›› እግዚአብሔርን በጥቂቱ እንዳታውቁት ሌላ ብዙ የከበረ እቅድ እና ፕሮግራም ለናንተ አለው:: በቅድስናና ያለ ነውር እንድትሆኑ ታስቦ ነው በክርስቶስ የተፈጠራችሁት፣ ስለዚህ ነውርን አርቁ::

እግዚአብሔር በሰማይ ያዘጋጀላችሁ ስፍራ የከበረ ነው እና ነገራችሁን ምድራዊ በሆነ ከንቱ ነገር አትለኩት፡፡ የጌታ የሃይሉ ታላቅነት የቱን ያህል እንደሆነ እወቁ እንጂ አትፍሩ፣ አትደንግጡ፡፡ የትንሳኤው ሃይል ሙታንን ያስነሳ፣ መቃብርን የፈነቀለ ዲያቢሎስን የረታ ነውና በጌታ ታመኑ፣ ጽኑ::

የሽንፈት ኑሮ አትኑሩ! ጌታን ማወቃችሁ መልካም ነው፣ ነገር ግን ሌላ ክብር አለ! ሌላ እውቀት አለ! ሌላ ከፍታ አለ! ያን ለማየት ደግሞ የልቦናችሁ አይኖች እንዲከፈቱ ያስፈልጋል::

ወገኖቼ፣ ይህ ደብዳቤ አሁን የኛ ደብዳቤ ነው:: በዚህ ዘመን ለምንኖር አማኞች የተጻፈ መልእክት ነው! የተጠራንበት አላማ ሊገባን ያስፈልጋል:: ከመብላት፣ ከመጠጣት፣ ከመልበስ ያለፈ የዘላለም ክብር እግዚአብሔር ለእኔ እና ለእናንተ እንዳለው መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ስብከታችን፣ መልእክታችን፣ ኑሮአችን ምድርን ያማከለ እንዳይሆን፣ የልቦናችን አይኖች ተከፍተው፣ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንደሆነ ልናውቅና ልንረዳ ያስፈልጋል!
--------------------------------

(ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክ ያድርጉ፣ ጌታ ይባርክዎ!)

Thursday, February 26, 2015

መንፈስ የሆነው ቃል!

ዲቮሽን .169/07፣ ሐሙስ የካቲት 19/07 ..
(
በዶ/ር በቀለ በላቸው)


መንፈስ የሆነው ቃል!

… ከአፌ የሚወጣ ቃሌ … የምሻውን ያደርጋል የላክሁትንም ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም (ኢሳ 5510-11)

የእግዚአብሔር ቃል እጅግ ብዙ ሥራን ይሠራል፡፡ የጌታ መንፈስ በነቢዩ ኢሳይያስ ከእኔ የሚወጣው ቃል፣ መንፈስ የሆነው ቃል፣ ወይም የጊዜው ቃል፣ የምሻውን ያደርጋል፣ የላክሁትን ይፈጽማል እንጂ ወደ እኔ በከንቱ አይመለስም (ኢሳይያስ 5510-11) ብሎ ተናግሯል፡፡

እውነት ነው መንፈስ የሆነው ቃል ከእግዚአብሔር አፍ ይውጣ እንጂ በከንቱ አይወድቅም፡፡ የዕብራውያን ጸሐፊ የእግዚአብሔርን ቃል ሲገልጸው የሚሠራ እና ሁለት አፍ ካለው ሰይፍ ይልቅ የተሳለ እና ወደ ጠለቀው ማንነታችን ዘልቆ ልባችንን እንደሚመረምር እና በእርሱ ፊት ሁሉ ነገር የተገለጠ እና የተራቆተ (ዕብራውያን 412-16) እንደ ሆነ ይናገራል፡፡

አዎ ትክክል! የእግዚአብሔር ቃል የሚሠራ ነው፣ ነፍስን ይመልሳል፣ ሰላምንና ደስታን ይሰጣል፣ ከብዙ ጥፋት ያወጣል ያድናልም፣ መንገድንም ያቀናል፡፡ በግሌ የቃሉን ኃይል በሕይወቴ አይቼዋለሁ፡፡ መንፈስ የሆነው ቃል ከብዙ ጉድ ሊያወጣን እንደሚችል በድፍረት መናገር እችላለሁ፡፡ በተግባር ደረጃ ይህ የሕይወት ቃል ወደ ውስጤ በመግባቱ ከመጠጥ፣ ከጫት፣ ከሲጋራ ሱስ እና ብልሹ ከሆነ ማኅበራዊ ሕይወት መንጭቆ አውጥቶኛል፡፡

እጅግ በጣም ይገርማል፡፡ እላዬ የነበረው የሱስ ቀንበር ቀላል አልነበረም፡፡ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን፤ ይህ ኃይል ያለው ቃል ነፃ አድርጐኝ፣ ተለቅቄ ያለ ምንም ባርነት እየኖርኩ እገኛለሁ፡፡ ወደ እሱ ከመጣሁ በኋላም ተነግሮ የማያልቅ ሥራን በሕይወቴ እየሠራ ይገኛል፡፡

ይህ የሚሠራ ቃል የጠላትን ተግዳሮት እንድናሸንፍ ያደርገናል፤ መጽሐፉ እንዲህ ይላልና፡-“ኃያል ሆይ፣ ፍላጻዎችህ የተሳሉ ናቸው፤ እነርሱም በንጉሥ ጠላቶች ልብ ውስጥ ይገባሉ፤ አሕዛብም በበታችህ ይወድቃሉ።” (መዝሙር 455) ይህ ምንባብ የሚናገረው እንደ ተሳለ ፍላጻ፣ በመንፈስ የሚነገር ቃል የሚያመጣውን ውጤት ነው፡፡

አዎ! በሕይወታችን መንፈስ የሆነው ቃል ማንኛውንም ተግዳሮት ጥሶ የመግባትና ነገሮችን የመለወጥ ችሎታ አለው፡፡

ነገር ግን እዚህ ሊታሰብ የሚገባው ጉዳይ፣ ወደ ውስጣችን በተለያየ መንገድ የሚገባው ቃል እንዴት ይሳላል የሚለው ነው፡፡ በጆሮአችን የምንሰማቸውና በዓይናችን የምናነባቸው የእግዚአብሔር መዛግብቶች፣ ወደ ልባችን የሚያልፉት በአእምሮአችን በኩል ነው፡፡

ለቃሉ ያልተከፋፈለ ልብን በመስጠት ስናጠናውና ስናሰላስለው፣ ብሎም በተግባር ደረጃ ስንለማመደው፣ በልባችን ጽላት ላይ በማይረሳ መልኩ ይጻፋል፤ ከሕይወታችን ጋር በሚገባ ይዋሃዳልም፡፡

ታዲያ ቃሉ በውስጣችን በእምነት ሲዋሃድ ተሳለ ማለት ይቻላል፡፡ ይህ የተሳለ ቃል ነው አሸናፊና ባለ ድል የሚያደርገን! ስለዚህ ለቃሉ ያልተከፋፈለ ልብን እንስጥ !
--------------------------------

(ትምህርቱ ጠቅምዎታል? እንግዲያውስ ላይክ ያድርጉ፣ ጌታ ይባርክዎ!)