Friday, October 31, 2014

የሰላም ወንዝ!



ዲቮሽን ቁ.51/07     አርብ፣ ጥቅምት 21/07 ዓ.ም.
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


የሰላም ወንዝ!

ታዳጊህ፥ የእስራኤል ቅዱስ፥ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። እኔ የሚረባህን ነገር የማስተምርህ በምትሄድባትም መንገድ የምመራህ አምላክህ እግዚአብሔር ነኝ። ትእዛዜን ብትሰማ ኖሮ፥ ሰላምህ እንደ ወንዝ ጽድቅህም እንደ ባሕር ሞገድ በሆነ ነበር (ኢሳ 48፡17-18)

ወዳጄ ሆይ፣ የወንዝ አፈሳሰስ ቆም ብለው አስተውለው ያውቃሉ! ወንዝ ከላይ ወደታች ይወርዳል! ጧትም ሆነ ማታ ሳያቋርጥ ይፈስሳል! ከእግዚአብሔር የሆነ ሰላም ጠዋትና ማታ ሳያቋርጥ በሚፈስስ ወንዝ ይመሰላል! እውነተኛ ሰላም ከእግዚአብሔር የሆነ ሰላም ነው! ከእግዚአብሔር የሆነ ሰላም ጠዋትና ማታ ሳያቋርጥ፣ ከላይ ወደታች ይፈስሳል!

ወዳጄ ሆይ፣ ወንዝ ፍሰቱ የሚቀንሰው ወይንም የሚደርቀው ድርቅ የመጣ እንደሆነ ወይንም ወደወንዙ ቆሻሻ የሚጣል ከሆነ ብቻ ነው! መንፈሳዊ ድርቅ ከክርስቶስ ያገኘነውን ሰላም ሊቀንሰው ወይንም ሊያደርቀው ይችላል! የሰላማችን ምንጭ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው! ዓለማዊነት ወደ ሕይወታችን መግባት ሲጀምር ይህ ሰላም ሊደፈርስ፣ ሊደርቅ ይችላል! 

ወዳጄ ሆይ፣ ጠዋትና ማታ የማያቋርጥ ሰላም መጎናጸፍ ይፈልጋሉ? ከነፍስዎ ሞልቶ ወደ ውጭ የሚፈስስ እውነተኛ ሰላም እንዲኖረዎ ይመኛሉ? እንግዲያውስ ከጌታ ለመማር ራስዎን ያዘጋጁ! የሚሰጥዎትን ትምህርት፣ የሚሰጥዎትን የቤት ሥራ፣ የሚሰጥዎትን ፈተና በትጋት ይወጡ! ቀሽም ተማሪ አይሁኑ! 

ወዳጄ ሆይ፣ የሰላምን መንገድ ከጌታ ይማሩ! የደስታን መንገድ ከጌታ ይማሩ! የማይረባን አስጥሎ የሚረባን ለሚያስይዝ ለታላቅ መምህር ሁለንተናዎን ይስጡ!  የእውነተኛን ደስታ መርቶ የሚያሳየውን ጌታን ይከተሉ! 

ወዳጄ ሆይ፣ የክርስቶስ ሰላም ከውስጣችን በሙላት እንዲፈስስ መንፈሳዊ ሕይወታችንን በየዕለቱ ልንንከባከብ ይገባል! ይህ ሲሆን ብቻ ነው፣ ‹‹ሰላም አለኝ እንደ ወንዝ የሚፈስስ፣ አዕምሮዬን የሚያረሰርስ፣ ደስታ አለኝ ከውስጤ የማይጠፋ፣ ኢየሱስ ክብሩ ይስፋ›› እያልን የምንዘምረው ዝማሬ እውነት የሚሆነው! 

-------------------------
(ይህን ዕለታዊ ዲቮሽን ላይክና ሼር ያድርጉ፣ ወዳጅ ጓደኞችዎም እንዲያገኙ ያግዙ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!)

No comments:

Post a Comment