Thursday, October 30, 2014

ተንኮታኩቶ መውደቅ!



ዲቮሽን ቁ.50/07     ሐሙስ፣ ጥቅምት 20/07 ዓ.ም.
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


ተንኮታኩቶ መውደቅ!

አህያይቱም የእግዚአብሔርን መልአክ አየች፥ ከበለዓምም በታች ተኛች በለዓምም እጅግ ተቈጣ፥ … እግዚአብሔርም የአህያይቱን አፍ ከፈተ፥ በለዓምንም። ሦስት ጊዜ የመታኸኝ ምን አድርጌብህ ነው? አለችው። እግዚአብሔርም የበለዓምን ዓይኖች ከፈተ የእግዚአብሔርን መልአክ በመንገድ ላይ ቆሞ የተመዘዘም ሰይፍ በእጁ ይዞ አየ ሰገደም፥ በግምባሩም ወደቀ።… በድያለሁ አንተ በመንገድ ላይ በፊቴ እንደቆምህብኝ አላወቅሁም እንግዲህም አሁን አትወድድ እንደ ሆነ እመለሳለሁ አለው። የእግዚአብሔርም መልአክ በለዓምን፦ ከሰዎቹ ጋር ሂድ፥ ነገር ግን የምናገርህን ቃል ብቻ ትናገራለህ አለው…(ዘሁ 22፡27-35)


ሰው የፈለገውን መንገድ መርጦ የመጓዝ ነጻ ፈቃድ አለው፡፡ እግዚአብሔር የሰውን ነጻ ፈቃድ በጉልበት አይጠመዝዘውም፡፡ ሆኖም የሰው ነጻ ፈቃድ በእግዚአብሔር እቅድ ላይ በተጽዕኖ በሚነሳበት ጊዜ እግዚአብሔር የራሱን እርምጃ ከመውሰድ ወደኋላ አይልም፡፡ 

እግዚአብሔር ሰውን ከራሱ መንገድ ለመመለስ ሲፈልግ የሚወስደው የመጀመሪያው እርምጃ መንገድ መዝጋት ነው፡፡ ሁለተኛው እርምጃ አጣብቂኝ ውስጥ ማስገባት ነው፡፡ ሦስተኛው እርምጃ ትምክህትን ከነድጋፉ አንኮታኩቶ መጣል ነው! 

በለዓም ለተሰጡት ሁለት ማስጠንቀቂያዎች አዎንታዊ ምላሽ አልሰጠም፡፡ በመሆኑም፣ ከቦታ ወደቦታ ለሚያደርጋቸው ጉዞዎች ሙሉ ድጋፉ የሆነችውን የአህያውን ጉልበት ያዘና ጣለበት! ምርኩዙ ተሰብሮ ስለወደቀበት በለዓም ለመቆም ተገደደ!  

ወገኖች ሆይ፣ የጤርሴሱን ሳውል አስቡ! በደማስቆ መንገድ ላይ ምርኩዙ ሲሰበር ነው ቀጥ ብሎ የቆመው! ናቡኬደነጾርን አስቡ! አርፎ እንዲቀመጥ ሲነገረው አሻፈረኝ ብሎ የንጉሥነት ማዕረጉ ተገፎ፣ ከሰውነት ተራ ወጥቶ እንስሳ ሲሆን ነው ቀጥ ብሎ የቆመው! 

ታውቃላችሁ፣ አንዳንዴ ክብር አይወድልንም! መከራና ችግር ሾጥ ሾጥ ካላደረገን ነገር አይገባንም! እሳት ለመያዝ እንደሚፈልጉ ሕጻናት፣ ሲከለከሉም እንደሚያለቅሱ ሁሉ  የሚጎዳንን ለመያዝ ትግል እናደርጋለን! 

ታውቃላችሁ፣ ‹‹ምከረው፣ ምከረው፤ እንቢ ካለ መከራ ይምከረው›› እንዲሉ ባለመመከራችን ችግር እንቀምሳለን! በገዛ እጃችን እሳቱን ለኩሰን፣ አንድደን አፏፍመን እንቃጠላለን! በሠራነው ስህተት እንጎዳበታለን! ለእምቢተኝነታችን ዋጋ እንከፍላለን! 

ወገኖች ሆይ፣ መስማት ከፈለግን ጌታ ይናገራል! በቃል፣ በነቢያት፣ በወቅቱ ሁኔታ፣ በወጀብ፣ በአውሎ ንፋስ ጌታ ይናገራል! ማዳመጥ ከቻልን ሁኔታዎቻችን አፍ አውጥተው ጮኸው ይናገራሉ! ማየት ከፈለግን ዓይኖቻችንን ይከፍታል! ዓይኖቻችን ከፍቶ ራሱን ያሳየናል! በመንገዳችን ያለውን፣ ከፊት የሚመጣውን፣ ተደብቆ ያለውን፣ ያልተገለጠውን … ገልጦ ያሳየናል!

ወገኖች ሆይ፣ ባልተፈቀደ መንገድ ገብተን እንዳንዳክር፣ የማይወድደውን እንዳንሞክር ጌታ ይርዳን! መንገዳችን ሲዘጋ ወደ መንገዱ እንድንዞር፣ አጣብቂኝ ውስጥ ስንገባ ራሳችንን እንድንመረምር፣ መርኩዛችን ሲሰበር ጌታን እንድንይዝ ጸጋው ይደግፈን! 

-------------------------
(ይህን ዕለታዊ ዲቮሽን ላይክና ሼር ያድርጉ፣ ወዳጅ ጓደኞችዎም እንዲያገኙ ያግዙ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!)

No comments:

Post a Comment