Tuesday, October 28, 2014

ጥሪና – ዝንባሌ!



ዲቮሽን ቁ.48/07     ማክሰኞ፣ ጥቅምት 18/07 ዓ.ም.
(በመጋቢ ተስፋሁን ሐጢያ)


ጥሪና – ዝንባሌ!

ሙሴ ካደገ በኋላ የፈርዖን የልጅ ልጅ እንዳይባል በእምነት እምቢ አለ፤ ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና (ዕብ 11:24-26


ጥሪና ዝንባሌ እንደ አንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው! ዝንባሌ አብሮ ተወልዶ አብሮ የሚያድግ ተሰጥኦ ነው፡፡ ማናቸውም ዓይነት ትምህርትና ሥልጠና ተሰጥኦን ሊተካ አይችልም፡፡ ማናቸውም ዓይነት የሕይወት ከፍታ ዝንባሌን አያረካም፡፡ በተጠራንበት ነገር አቅጣጫ እስካልተሰማራን ድረስ እፎይታ አይገኝም፡፡

ታውቃላችሁ፣ ሙሴ የግብጾችን ጥበብ ሁሉ የተማረ የተመራመረ (የሐዋ 7፡22) ቢሆንም፣ በቤተመንግሥት የሚኖር ልዑል ቢሆንም፣ የተጠራበት ነገር አለና አርፎ መቀመጥ አልቻለም! ስለሆነም፣ ከቤተመንግሥት ድሎት ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ!

ታውቃላችሁ፣ ሺህ ጊዜ ሺህ ድሎት፣ እልፍ ጊዜ እልፍ ሀብት ቢኖር ወደተጠራንበት መስመር ካልገባን በስተቀር፣ በተጠራንበት ሥራ እስካልተሰማራን ድረስ እፎይታ አይገኝም!

ታውቃላችሁ፣ ዝንባሌያችንን ተከትለን እስካልሠራን ድረስ፣ በሕይወታችን ውስጥ እርካታ አናገኝም፡፡ ጥሪያችንን ተከትለን እስካልተሰማራን ድረስ እፎይታ አይኖረንም!

ታውቃላችሁ፣ ሰው በራሱ ጥረት የእግዚአብሔርን ጥሪ ማግኘት አይችልም! ነገር ግን ለእግዚአብሔር የሚቀና መንፈስ ያለው ሰውና ዘወትር ለሕዝቡ የሚቆረቆር ሰው ሳይታወቀው ራሱን የእግዚአብሔር መልዕክተኛ ሆኖ ያገኘዋል!

ታውቃላችሁ፣ እግዚአብሔር ለአንድ ነገር ጠርቶን ከሆነ አእምሮአችን ስለተጠራንበት ስለዚያ ጉዳይ ቀንና ማታ እየተጨነቀ እረፍት አያገኝም፡፡ በትንሽ ቅልቁ ነገር ሁሉ ሆድ እየባሰን እንታወካለን! ስለጉዳዩ ላለማሰብ እንኳ ብንወስን አይሳካልንም! ከጉዳዩ መሸሽ መራቅ ብንፈልግ የትም አናመልጥም!

ወዳጄ ሆይ፣ በአካባቢዎ በሚሠራው ክፉ ነገር ምክንያት ሁልጊዜ በውስጥዎ እረፍት የማይሰማዎ ከሆነ በሕይወትዎ አንድ ነገር እየሆነ ነው! በኃጢአት ላይ መንፈስዎ የሚቆጣ፣ የሚበሳጭ፣ የሚረበሽ፣ የሚያለቅስና የሚቃወም ከሆነ እርስዎ የእግዚአብሔር መልዕክተኛ መሆንዎትን ይወቁ! መንፈስዎ በሚበሳጭበት ነገር አቅጣጫ ጥሪ እንዳለዎ ይመኑ! ያመኑበትን ጥሪ ይቀበሉ! ለተቀበሉትም ጥሪ ተገቢ ምላሽ ይስጡ!

-------------------------
(ይህን ዕለታዊ ዲቮሽን ላይክና ሼር ያድርጉ፣ ወዳጅ ጓደኞችዎም እንዲያገኙ ያግዙ፡፡ ጌታ ይባርክዎ!)

No comments:

Post a Comment