Tuesday, April 28, 2015

ሰይፍ የሚያነሡ - በሰይፍ ይጠፋሉ!

ዲቮሽን 230/07፥ ማክሰኞ፥ ሚያዝያ 20/07 ዓ/ም
(በፓ/ር ተስፋሁን ሐጢያ)


ሰይፍ የሚያነሡ - በሰይፍ ይጠፋሉ!

ከኢየሱስ ጋር ከነበሩት አንዱ እጁን ዘርግቶ ሰይፉን መዘዘና የሊቀካህናቱን ባሪያ መትቶ ጆሮውን ቆረጠው፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ እንዲህ አለው፥ "ሰይፍ የሚያነሱ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋሉና ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ" (ማቴ 26፡51-52)

ወገኖች ሆይ፥ ኢየሱስን ተመልከቱ! ጌታችን ኢየሱስ ቀጭን ትዕዛዝ ቢሰጥ፥ የሰማይ ሠራዊት ከጸሐይ ፍጥነት ይልቅ ፈጥነው ሊደርሱለትና የተነሱበትንም ኃይሎች ሊደመስሱትና ሊያጠፉም በቻሉ ነበር! ነገር ግን ያንን መድረግ አልፈለገም! ራሱን ለመከላከልም፥ ጋሻ ጦርና ሰይፍ ፍጹም አልታጠቀም! ለዚህም ነው ጴጥሮስን መገሰጽ የቻለው!

ታውቃላችሁ፥ ጴጥሮስ የማልኮስን ጆሮ ቆርጦ ሲጥል፥ ጌታችን ኢየሱስ ጴጥሮስን ገስጾ፥ የማልኮስን ጆሮ መልሶ ፈወሰ፡፡ ወገኖች ሆይ፥ የክርስትና እምነት የሰይፍና የጦር ድጋፍ አይፈልግም! የክርስትና ሐይማኖት ጠላቶችን መውድድ፥ የሚረግሙትን መባረክ እንጂ፥ የእኔን እምነት ካላመንክ፥ የኔን መንገድ ካልሄድክ ብሎ የሰውን ጆሮ መቁረጥ፥ የሰው አንገት ማረድ በክርስትና ዓለም እንዲህ ያለ የለም!

ታውቃላችሁ፥ የክርስትና እምነት እውነት ስለሆነ፥ የጦር የሰይፍ ድጋፍ አያስፈልገውም! የክርስትና እምነት የሠራዊቱን ጌታ ሕያው እግዚአብሔርን የሚያመልክ ስለሆነ፥ ይህን እምነት በዓለም ለማስፋፋት የሰው ጡንቻና ኃይል አያስፈገውም!

ወገኖች ሆይ፥ ጌታችን ኢየሱስ ለጴጥሮስ ሲናገር፥ የሰማዩ አባቴ ብጠይቀው ከ12 ጭፍሮች(ከ72ሺ) የሚበልጡ መላዕክት ሊሰድድልኝ እንደሚችል አታውቅምን? ያለው ታላቅ ትምህርት አለው፡፡
ወገኖች ሆይ፥ በሮማ ዘመነ መንግሥት አንድ ጭፍራ (ሌጊዮን) 6ሺ ወታደሮችን ይይዛል፡፡ በዚህ ስሌት መሠረት፥ ጌታ 12 ጭፍሮችን(ሌጊዮኖችን) ማለትም 72ሺ መላዕክት ማዘዝ ይችል ነበር፡፡ ይህን አላደረግም፡፡ ነገር ግን፥ ይህን ቢያደርግ ኖሮ ምን ይፈጠር ነበር?

ወገኖች ሆይ፥ በግብጽ ሀገር አንድ መልዐክ ባንዲት ሌሊት ብቻ፥ የተቀረቀሩ በሮች መስበር ሳያስፈልግ፥ የተዘጉ ደጆች መክፈት ሳያስፈልግ፥ ከቤተ መንግሥቱ እስከ ጥበቃ ድረስ (ዘጸ 12፡23) ማንም ሳያግደው ማንም ሳይቋቋመው የግብጽን በኩራት ለመግደል መቻሉን ልብ ያለው ልብ ይሏል!
ወገኖች ሆይ፥ እስራኤልን በመቁጠር ዳዊት በፈጸመው ጥፋት አንዱ መልዐክ ብቻ፥ በአንዲት ቀን ብቻ (2ሳሙ 24፡15-17) 70ሺ እስራኤላዊያን መጨረሱን አሁንም ልብ ይሏል!

ወገኖች ሆይ፥ በሕዝቅያስ ዘመን የአሶር ንጉስ ሴናክሬም በትዕቢት ተነስቶ በእስራኤላዊያን ላይ ሠራዊት ሰብስቦ ሲመጣ፥ አንዱ መልዐክ ብቻ፥ በአንዲት ቀን ብቻ (2ነገ 19፡35) 185ሺ አሶራዊያንን መደምሰስ መቻሉን አሁንም ልብ ይሏል!

ታውቃላችሁ፥ ጌታ ከተዋጋ፥ አንዱ መልዐክ ብቻ፥ የፔንታጎንንና የተባበሩት መንግሥታት የጦር ኃይሎቻቸውን፥ የባህር ኃይሎቹን የምድር ተዋጊዎቹን፥ ሚሳይሎቻቸውን፥ ሚጎች መናምኖች፥ ድሮኖቻቸውን በመብረቅ ብልጭታ፥ በሰከንዶች ፍጥነት ድባቃቸውን መትቶ፥ ድራሻቸውን ሁሉ ሊያጠፋ ይችላል!

ታውቃላችሁ፥ ጌታችን ኢየሱስ የቁጥራቸውን ብዛት፥ የሰው ቋንቋ ስሌት ሊገልጽ የማይችለውን የሰማይ መላዕክት ፈጣሪና አዛዥ ተቆጣጣሪያቸውም ነው! ይህንን ኃይል ይዞ፥ ይህን ጉልበት ይዞ፥ ሲወጉት ሲወግሩት፥ በእንጨት ላይ ሲሰቅሉት የሚያደርጉትን ነገር ምንም ለማያውቁ፥ በመንፈስ ጭለማ ለሚመላለሱ ለሐይማኖት መሪዎች፥ ሰይፍና ጦር ይዘው ሲሰድቡት፥ ሲያዳፉት፥ ሲያንገላቱትም ለነበሩ ለሮማዊያን ጭፍሮች ምሕረትን ለመነ፡፡

ወገኖች ሆይ፥ ይህ ነው ፍቅር ማለት! ይህ ነው እምነት ማለት! መመካት ቢያስፈልግ ደግሞ ይህ ነው ክርስትና፥ ይኼ ነው ሐይማኖት!

ወገኖች ሆይ፥ በጦርና በሰይፍ የሚስፋፋ ሐይማኖት፥ ጤና የሌለው ነው! ሀገር በማሸበር፥ የሰው ደም በማፍሰስ የሚያስፋፉት ሐይማኖት ከአጋንንት አምልኮ የተሻለ ቦታ ሊሰጠው አይችልም! የሰውን ልጅ በማረድ የሚደሰት መንፈስ ከአጋንንት እንጂ ከሰው ልጅ አይደለም!

ወገኖች ሆይ፥ ጌታችን ኢየሱስ የወንጌን እምነት እንድናስፋፋ ያስተማረን በፍቅር ብቻ ነው! ወንጌል ስንመሰክር፥ እንደ በጎች ወደ ተኩላዎች መሀል ሰተት ብለን ገብተን፥ የእግዚአብሔርን ፍቅር በሰው ልጆች መሃል ተግተን እንድናስፋፋ ተልዕኮ ሰጥቶናል፡፡ ይኼ ነው እውነቱ፥ ይህ ነው እምነት ማለት፥ መመካት ቢያስፈልግ ይኼ ነው ሐይማኖት!

ሰይፍን የሚያነሱ - በሰይፍ ይጠፋሉ! በሐይማኖት ሰበብ ሰውን የሚገድሉ ሲዖል ይገባሉ!

No comments:

Post a Comment